1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

ሀገራዊ መፍትሔ አፈላላጊ ግብረ ኃይል እንዲቋቋም “ኢትዮጵያን የማዳን መድረክ” ጥሪ አቀረበ

ቅዳሜ፣ ታኅሣሥ 20 2016

ኢትዮጵያን እጅግ ከከፋ የእርስ በርስ ጦርነት ይታደጋል ያሉትን ፍኖተ ካርታ ይፋ ማድረጋቸውን፣ኢትዮጵያን የማዳን መድረክ በሚል የተሰባሰቡ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን አስታወቁ። ሀገራዊ መፍትሔ አፈላላጊ ግብረ ኃይል እንዲቋቋም ጥሪ አቅርበዋል። “በሕዝብ የተመረጠ ዴሞክራሲያዊ መንግሥት ማቋቋም” የግብረ ኃይሉ የመጨረሻ ግብ ነው ተብሏል

የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ
ኢትዮጵያን እጅግ ከከፋ የእርስ በርስ ጦርነት ይታደጋል ያሉትን ፍኖተ ካርታ ይፋ ማድረጋቸውን፣ኢትዮጵያን የማዳን መድረክ በሚል የተሰባሰቡ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን አስታወቁ።ምስል፦ AMANUEL SILESHI AFP via Getty Images

የሀገራዊ መፍትሔ አፈላላጊ ግብረ ኃይል እንዲቋቋም “ኢትዮጵያን የማዳን መድረክ” ጥሪ አቀረበ

This browser does not support the audio element.

የፍኖተ ካርታው አዘጋጆች፣ለረጅም ጊዜ በኢትዮጵያና በውጭ ሃገራት የስራ ልምድ ያካበቱ፣ በትምህርት ደረጃም በየዕርከኑ በቂ ዕውቀትና  ስልጠና ያላቸው ኢትዮጵያዊና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን መሆናቸው ተመልክቷል።

በኢትዮጵያ የሚካሄደው የእርስ በርስ እልቂትና መዘዞቹን በመረዳትና የሃገሪቱን መጻኢ ዕድል ምን ሊሆን እንደሚችል በስጋት በማሰብ፣ ሰነዱን ለማዘጋጀት መነሳታቸውን በበይነ መረብ በተካሄደው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተገልጿል።

ባለፉት 63 ዓመታት ያህል በጥፋት ላይ ጥፋት የነበረው ጉዞ፣ ኢትዮጵያን ለከፋ ችግር እንደዳረጋት፣የመድረኩ አባል ዶክተር ሰለሞን ወልደአብ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ አስረድተዋል።

ኢትዮጵያ ጦርነት፣አሜሪካና የምሁራን አስተያየት

"የኢትዮጵያ መሰረታዊ ችግሮች ህገ መንግስታዊ፣ መዋቅራዊና ሥርዓታዊ ናቸው ነው የሚባሉትና እነዚህን እድሎች ሲያመልጡ፣ምን ሊቀይሩ መጥተው ምን አመለጠ የሚለው ነገር የዚህ ሰነድ አዘጋጆች፣በራሳቸው እነዚህ ናቸው ያመለጡ አንኳር አንኳር  ዕድሎች ናቸው በማለት ለማቅረብ ሞክረዋል" ሲሉ ዶክተር ሰለሞን ተናግረዋል። 

ለአካታች መንግስት ምስረታ ያመለጡ ዕድሎች በማለት፣ዶክተር ሰለሞን ከጠቀሷቸው መኻከል፣የ2010-2011 ዓ.ም ሕዝባዊ አመጽ፣የ1997 ምርጫ፣በ1983 የተደረገው የመንግስት ለውጥና በ1966 የተቀጣጠለው ሕዝባዊ አመጽ ይገኙባቸዋል።

ኢትዮጵያ አሁን በተጋረጡባት ፈተናዎች፣ እንደ ሀገር እንዳትጠፋ ማድረግ አለብን ያሉት ሌላው የመድረኩ አባል ዶክተር አቻምየለህ ደበላ በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ በመስቀለኛ  መንገድ ላይ የምትገኝበትን ሁኔታ አብራርተዋል።

ኢትዮጵያን የማዳን መድረክ የተባለው ስብስብ እንዲቋቋም የጠየቀው ሀገራዊ መፍትሔ አፈላላጊ ግብረ ኃይል የመጨረሻ ግብ “በሕዝብ የተመረጠ ዴሞክራሲያዊ መንግሥት ማቋቋም” ነው ተብሏልምስል፦ Ben Curtis/AP Photo/picture alliance

በሃገሪቱ አሁን የሚታየው ነባራዊ ሁኔታ፣በዚሁ ከቀጠለ ሊሆኑ ስለሚችሉ አደጋዎች ዶክተር አቻምየለህ "መንግስት በተለያዩ ምክንያቶች ለድርድር ዝግጁ ሳይሆን ከቀረ፣ ሰላማዊ የሆነው መንገድ ሁሉ ተዘግቶ፣ችግሮችን በጦርነት ብቻ ለመፍታት የሚደረገው ሙከራ ይቀጥላል።ህዝቡም ውጊያውን በስንቅና በሚችለው ይተባበራል። በአጭሩ መቶ ሺህ በሚሆነው መከላከያ ላይ ከ30 እና 40 ሚሊዮን ህዝብ በላይ ጋር ይገጥማል ማለት ነው" ሲሉ አስረድተዋል።

 የሽግግር ፍትሕ የፖሊሲ አቅጣጫ የመጨረሻ ውጤት ይፋ ሆነ

ፍኖተ ካርታውን ያዘጋጁት የመድረኩ አባላት፣ ኢትዮጵያን ከአስከፊ ሁኔታ ለማዳን፣የሃገራዊ መፍትሄ አፈላላጊ ግብረ ኀይል ምስረታን በመፍትሔነት አቅርበዋል። በአሜሪካ ሞርጋን ስቴት ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ ፕሮፌሰር  ጌታቸው መታፈሪያ "ግብረ ሃይሉ የሚሰራው ወደመጨረሻው ላይ፣ ሰላማዊ የሆነ በህዝብ የተመረጠ ዲሞክራሲያዊ መንግስት ማቋቋም ነው።ከዚያ በፊት ግን የሃገራዊ መፍትሄ አፈላላጊ ግብረ ኀይሉ ሁሉንም አሳታፊ በሆነ መልኩ ይሰበሰብና አንድ የስድስት ወር ጊዜ ተሰጥቶት በእዛ ውስጥ ሁኔታዎችን በየፈርጁ እያስቀመጠ መፍትሄ እየፈለግለት ይሄዳል" ብለዋል። 

ለዚህ ሃገራዊ ጥሪ የኢትዮጵያ መንግስት አዎንታዊ ምላሽ እንዲሰጥ የጠየቁት የመድረኩ አባላት፣ያን አለማድረግ ማለት በታሪክ የሚያስጠይቅ ከመሆኑም በላይ ሃገሪቱን ለከፋ ችግርና አደጋ መዳረግ መሆኑን አመልክተዋል። ስለፍኖተ ካርታው ዋሽንግተን ዲሲ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ አስተያየት ለማግኘት ጥረት ብናደርግም ለጊዜው ምላሽ አላገኘንም።

ታሪኩ ኃይሉ 

እሸቴ በቀለ


 

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW