ለማርስ ጉዞ፣ የዝግጅት መፈተሻ ምርምር፣
ረቡዕ፣ መጋቢት 23 2001ባለፈው ሳምንትም፣ ኅዋ፣ የቁሻሻ(የብረታ-ብረት ስብርባሪ መጣያም ሆነ ማከማቻ እንዳይሆን)ያለውን ሥጋት አስመልክተን መዘገባችን የሚታወስ ነው። ፕላኔታችን፣ በሰው-ሠራሽና በተፈጥሮ፣ ተፈታታኝ አደጋ ሊያጋጥማት እንደሚችልe እየታወቀም ህይወትን መደገፍ ይቻሉ-አይቻሉ፣ በውል ያልታወቀላቸውን ዓለማት ለማሰስ ዝግጅቱ ጋብ ያለ አይመስልም። ምድራችን፣ ከኅዋ፣ በሰው-ሠራሽና በስብርባሪ ከዋክብት የሚደቀንባትን አደጋ ለመግታት ዘላቂ ብልሃት የተገኘም አይመስልም።
Mars Lander የተባለችው መንኮራኩር ፣ ከአያሌ ወራት በፊት ስለማርስ ላቅ ያለ ግንዛቤ የሚያስጨብጡ መረጃዎች ካቀረበች ወዲህ፣ ስለሌሎች በተለይ ከምድር ጋር ተመሳሳይ ባህርይ ይኖራቸዋል ተብለው የሚታሰቡ ፕላኔቶችን ይበልጥ ማወቅ ይቻል ዘንድ ጠጋ አድርጎ የሚያሳይ «ኬፕለር» የተባለው 600 ሚሊዮን ዶላር ወጪ የተደረገበትና ቢያንስ 3 ዓመት ተኩል ተግባሩን የሚያካሂድ፣ ቴሌስኮፕ ከአንድ ወር ገደማ በፊት መላኩ ይታወሳል።
በትናንቱ ዕለት ደግሞ፣ በማርስ ላይ ትኩረት ያደረጉት ዓለም አቀፍ የምርምር ተቋማት ሞስኮ ውስጥ 105 ቀናት የሚወስድ ፣ ወደማርስ የሚላኩ ሰዎች በረጅም ጊዜ ጉዞ፣ ምን ሊያጋጥማቸው እንደሚችልና ከወዲሁም መፍትኄውን መሻት ይቻል ዘንድ ይረዳል ተብሎ የታመነበትን ሙከራ ጀምረዋል። ማርስ ድርሶ ለመመለስ፣ በአሁኖቹ የጠፈር መንኮራኩሮች ፍጥነት ፣ አንድ ዓመት ከ 155 ቀናት እንደሚወስድ እሙን ነው።
ተክሌ የኋላ፣
ነጋሽ መሐመድ፣