1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ለተበዳሪ ሃገራት የሚደረገው የብድር ስረዛ

sdestaሐሙስ፣ መስከረም 13 1997

ቡድን ሰባት በመባል የሚጠሩት በእንዱስትሪ የበለፀጉት ሃገራት በመጪው ሳምንት ሲሰበሰቡ የዕዳ ስረዛ ውሳኔ እንደሚያስተላልፉ ይጠበቃል ። ይህንን ዕቅድ የሚደግፉ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችም ለድሃ ሃገራት የተሰጠው ብድር ሙሉ በሙሉ እንዲሰረዝ ቅስቀሳ በማድረግ ላይ ይገኛሉ

ከተጀመረ ስምንት ዓመት ባስቆጠረው እና ዕዳ የተቆለለባቸው ሃገራት እንዲቀነስላቸው በተነደፈው ዓለም አቀፉ መርሃ ግብር መሰረት እስካሁን ሃያ ሰባት ሃገራት የዕዳ ቅነሳ ተደርጎላቸዋል ። ከነዚሁ ሃገራት ከአንድ ቢሊዮን ዕዳ ውስጥም ወደ ሰላሳ ቢሊዮኑ ዕዳ ተቀናሽ ሆኗል ። አብዛኞቹ ሃገራት የተበደሩትን ገንዘብ ለማህበራዊ አገልግሎት ከማዋል ይልቅ ብድርን ለመክፈል ይበደራሉ የሚሉት መንግስታዊ ያልሆኑት ድርጅቶች አሁን ግን ይህ መቆም አለበት ይላሉ ። በዩናይትድስቴትስ እና በብሪታንያ የተደገፈው እቅድ ያስደሰታቸው መሆኑን ገልጸዋል ። ከነዚሁ መካከል አክሽን አፍሪካ ፣ ኦክስፋም እና የህክምና ባለሙያዎች ለሰብአዊ መብት የተባሉት መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ይገኙበታል ።

የብድር ስረዛው እቅድ ዘግይቷል ያሉት የአክሽን አፍሪካ ዋና ዳይሬክተር ሳሊህ ቡከር እስካሁን የሚደረጉት የዕዳ ቅነሳዎች በቂ እንዳልነበሩ ይገልጻሉ ። በድሃ ሃገራት ላይ የሚቆለለው ዕዳ በተለይ በአፍሪካ የተስፋፋውን የኤች አይቪ በሽታ ስርጭት ከመቋቋም ይልቅ እያባባሰው ነው ብለዋል ። እሳቸው እንደሚሉት ሃገራቱ በሚያገኙት ገንዘብ የጤና ዘርፎችን እና አገልግሎቶችን ከማጠናከር ይልቅ ዕዳ ለመክፈል ይታትራሉ ። በመሆኑም ኤች አይቪ ኤይድስን ለማግታት የሚያደርጉትን ጥረት ያሳንሳል ። በድሃ ሃገራት ዘንድ ዕዳ ከሞት ጋር የተያያዘ ነው ያሉት የህክምና ባለሙያዎች ለሰብአዊ መብት የዋሽንግተን ቅርንጫፍ ዳይሬክተርም ይህንኑ ሃሳብ ያጠናክራሉ ። ዳይሬክተሯ ሆሊ ቡርካሃልተር በድሃ ሀገራት ላይ የተጫነው ዕዳ በችግር ላይ ያለውን የጤና ዘርፍ ችግር ውስጥ ከቶታል ብለዋል ። ዕዳው ሙሉ በሙሉ እንዲሰረዝ ለሚጠይቀው ደብዳቤም ከመላው ዓለም የአንድ መቶ ሃምሳ የህክምና ዶክተሮች ፊርማ ተሰባስቧል ።

የዕዳ ስረዛውን የደገፉ ሌሎች ተሟጋች ድርጅቶችም የዕዳ ስረዛው በሰላሳ ሶስት ሃገራት ብቻ መወሰን የለበትም ይላሉ ። እቅዱ ሁሉንም ተበዳሪ ሃገራት እንኳን ባይመለከት ቁጥሩ መጨመር ይገባዋል ሲሉ ጠይቀዋል ። ተሟጋች ድርጅቶቹ የዕዳ ስረዛው ውሳኔ መስተጓጎል የለበትም ለማለት የተነሳሱት ጉዳዩ በይበልጥ በዩናይትድስቴትስ ተደግፎ በመቅረቡ ነው ። የፕሬዝዳንት ጆርጅ ቡሽ አስተዳደር ባወጠው ይፋ መግለጫ ለድሃ ሃገራት በተለይ ለኢራቅ የብድር ዕዳው እንዲነሳላት ፍላጎቱን አንፀባርቋል ። ኢራቅ ከአንድ መቶ ቢሊዮን በላይ የብድር ዕዳ አለባት ። የኢራቅ የብድር ስረዛ ጥያቄ በመጀመሪያ የቀረበው ባለፈው ሰኔ በጆርጂያ በተካሄደው የቡድን ሰባት ስብሰባ ላይ በብሪታንያ ጠቅላይ ሚንስትር በቶኒ ብሌር ነበር ።

የዕዳ ስረዛው እቅድ በዩናይትድስቴትስ እና በብሪታንያ ቢደገፍም ለውሳኔ ለመብቃት ግን ችግር ሊገጥመው እንደሚችል በመጠቆም መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ስጋታቸውን ይገልጻሉ ። የስጋታቸው ምንጭ እየተነሳ ያለው ተቃውሞ ነው ። አበዳሪ የገንዘብ ተቋማቱ የዓለም ባንክ እና የዓለም የገንዘብ ድርጅት ዕዳን ሙሉ በሙሉ መሰረዝ አስቸጋሪ መሆኑን በመግለፅ ላይ ናቸው ። እንደ እነሱ ምክንያት በአንድ በኩል የገንዘብ ተቋማቱን የማበደር አቅም የሚፈታተን ይሆናል ። በሌላ በኩል ደግሞ ተበዳሪ ሃገራቱም ያላቸውን የተጠያቂነት ድርሻ የሚሽረሽር ነው ። ከዩናይትድስቴትስ እና ከብሪታንያ ውጭ ያሉት የቡድን ሰባት አባል ሀገራትም ተመሳሳይ እምነት እና አቋም ያንጸባርቃሉ ። የቡሽ አስተዳደር የብድር ስረዛውን በመደገፍ የኢራቅን ዕዳ ለማሰረዝ ለሽፋን ይጠቀምበታል የሚል እምነትም አላቸው ። በመሆኑም ለኢራቅ ሙሉ በሙሉ የዕዳ ስረዛ ሊደረግላት አይገባም የሚል አቋም እንደያዙ ይነገራል ። በተለይ የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ዣክ ሽራክ የዕዳ ስረዛ የሚያስፈልጋቸው የባሰባቸው ድሃ ሃገራት እያሉ ለኢራቅ ቅድሚያ ሊሰጣት አይገባም የሚል አቋም አላቸው ።

አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች የኢራቅ ወረራን ተከትሎ ከአትላንቲክ ወዲህ እና ከአትላንቲክ ማዶ ባሉት ሃገራት መካከል የነበረው ውጥረት በዕዳ ስረዛ ሳቢያ እንዳይባባስ በማለት ስጋታቸውን ገልፀዋል ። የብድር ስረዛውን እቅድ የደገፈው እና ‘’ ሃምሳ አመት ይበቃል ‘’ የተባለው ተሟጋች ድርጅት ይህንን ስጋቱን የገለፀው ዝሆኖች ሲጣሉ የሚጎዳው ሳሩ ነው በሚል ምሳሌያዊ አነጋገር ነው ። ድርጅቱ የገንዘብ ተቋማትን አበዳሪነት በመቃወም በየጊዜው ስሞታውን ያሰማል ። ይኸው ድርጅት አሁን ሊደረግ የታቀደው የብድር ስረዛ ልክ ብድር ለመስጠት ይቀርብ እንደነበረው ቅድመ ሁኔታዎች ሊበጅለት አይገባም ሲልም አሳስቧል ። ለሁሉም የዕዳ ስረዛው ዕቅድ የመጨረሻ ውሳኔ የቡድን ሰባት ሃገራት የገንዘብ ሚንስትሮች መስከረም ሃያ አንድ ሲሰበሰቡ ይለይለታል ።

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW