1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ለዘላቂ ሰላም የሲቪል ማኅበረሰቡ ሚና

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 17 2014

ኢትዮጵያ የጀመረችው ብሔራዊ ምክክር ዘላቂ ሰላም ማምጣት እንዲችል የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት እና የሲቪክ ማሕበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት በጋራ እየሠራን ነው አሉ። ሕዝብ የምክክሩ ባለቤት ሆኖ ብሔራዊ መግባባት የሚፈጥር ምክክር እንዲከናወን የድርሻቸውን እንደሚወጡም ገልፀዋል።

Äthiopien Addis Abeba | Treffen Organisationen der Zivilgesellschaft und politische Parteien
ምስል Solomon Muche/DW

«የሚሰቀጥጡ ነገሮች መቆም አለባቸው»

This browser does not support the audio element.

ኢትዮጵያ የጀመረችው ብሔራዊ ምክክር ዘላቂ ሰላም ማምጣት እንዲችል የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት እና የሲቪክ ማሕበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት በጋራ እየሠራን ነው አሉ። ሁለቱ ምክር ቤቶች የምክክር ሂደቱ ገለልተኝነት እንዳይለየውና ከተጽዕኖ እንዲላቀቅ፣ በሌላ በኩል ሕዝብ የምክክሩ ባለቤት ሆኖ ብሔራዊ መግባባት የሚፈጥር ምክክር እንዲከናወን የድርሻቸውን እንደሚወጡ ገልፀዋል።  የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ኢትዮጵያ ውስጥ በልሂቃን መካከል በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ መግባባት አለመኖሩ ፣በመካከላቸው ያለው አለመተማመን እና ጥርጣሬ የዴሞክራሲ የሽግግር ሂደቱን ፈታኝ በማድረጉ በሚል አስፈላጊነቱ ታምኖበት የተዋቀረና ወደ ሥራ የገባ እንደሆነ ይነገራል። ለዝርዝሩ የአዲስ አበባው ወኪላችን ሰለሞን ሙጬ።


የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት እና የኢትዮጵያ የሲቪክ ማኅበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ዛሬ ብሔራዊ ምክክሩ የታለመለትን ግብ እንዲመታ አጋዥ ሀሳብ ለማሰባሰብ ባዘጋጁት ውይይት ላይ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምክክር ለማድረግ ሁለት ዋና ዋና አስገዳጅ ሁኔታዎች አሉ ተብሏል። እነሱም ሥር ነቀል ማኅበረ ኢኮኖሚያዊ ለውጥ የማምጣት አስፈላጊነት እና የፖለቲካ ቀውስን የመከላከል እና የመቆጣጠ ግዴታ ናቸው ተብሏል። 

የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት የምክክር ኮሚሽኑን ለመምራት ከተሰየሙ ሰዎች የአመራረጥ ሂደት ጀምሮ የገለልተኝነት ጥያቄ ሲያነሳ ነበር። የጋራ ምክር ቤቱ ፀሐፊ ዶክተር ራሔል ባፌ ይህ ጉዳይ አሁንም በውይይት ሂደቱ በጥንቃቄ እንዲታይ የወከሏቸው ፓርቲዎች ፍላጎት መሆኑን ገልፀዋል። 

ኢትዮጵያ ብሔራዊ ምክክር በታሪኳ ኖራት አያውቅም። ከብሔራዊ የምክክር ኮሚሽነሮች አንደኛው አቶ መላኩ ወልደ ማርያም የኢትዮጵያ ሕዝብ የዚህ ጉዳይ ዋነኛ ባለቤት መሆኑን ተናግረዋል። ኮሚሽኑን እንዲቋቋም ያደረገው "አገራዊ አለመግባባትም መቆም አለበት" ብለዋል።

ምስል Solomon Muche/DW

በብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካ ፓርቲዎች እና ሲቪክ ማሕበራት ዘርፍ ኃላፊ ዶክተር አለሙ ስሜ «የብሔራዊ ምክክር ሂደቱ ከምንም እንከን ነፃ ሆኖ መተማመን እንዲኖር ትልቅ ሥራ ይጠብቀናል» ብለዋል።

ሌላኛው የብሔራዊ ምክክር ኮሚሽነር ዶክተር ዮናስ አዳዬ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዚህ ምክክር በተጨባጭ ምን ያገኛል ብለን ላቀረብንላቸው ጥያቄ «አዲስ የፖለቲካ ባህል  ያገኛል» በማለት መልሰዋል። እስካሁን ከትግራይ ክልል በስተቀር በሁሉም ክልሎች መጓዛቸውንም ገልፀዋል።

በውይይቱ እየበዛ የመጣው የክልል እንሁን ጥያቄዎች እና ፍላጎቶችን የመፍታት ቁርጠኝነት ለምክክሩ ስኬት ያለው ድርሻ እንዲጤን ተጠይቋል።በብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካ ፓርቲዎች እና ሲቪክ ማሕበራት ዘርፍ ኃላፊ ዶክተር አለሙ ስሜ «የብሔራዊ ምክክር ሂደቱ ከምንም እንከን ነፃ ሆኖ መተማመን እንዲኖር ትልቅ ሥራ ይጠብቀናል» ብለዋል።

ሌላኛው የብሔራዊ ምክክር ኮሚሽነር ዶክተር ዮናስ አዳዬ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዚህ ምክክር በተጨባጭ ምን ያገኛል ብለን ላቀረብንላቸው ጥያቄ «አዲስ የፖለቲካ ባህል ያገኛል» በማለት መልሰዋል። እስካሁን ከትግራይ ክልል በስተቀር በሁሉም ክልሎች መጓዛቸውንም ገልፀዋል።

በውይይቱ እየበዛ የመጣው የክልል እንሁን ጥያቄዎች እና ፍላጎቶችን የመፍታት ቁርጠኝነት ለምክክሩ ስኬት ያለው ድርሻ እንዲጤን ተጠይቋል።

ሰለሞን ሙጬ

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ሸዋዬ ለገሰ