መሻሻል አለበት የተባለው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፍትህ አገልግሎት
ሐሙስ፣ መስከረም 15 2018
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመልካም አስተዳደር እጦት ከሚታይባቸው መካከል አንዱ የፍትህ ዘርፍ ሥለመሆኑ በተለያዩ መድረኮች ላይ ሲጠቀስ ቆይቷል ፡፡ በክልሉ በሀላባ ቁሊቶ ከተማ ጉባዔውን ያካሄደው የክልሉ የዳኝነትና የፍትህ ዘርፍ ተቋማት ጥምረት የህዝቡን የፍትህ ጥያቄ ለመመለስ በትኩረት መሥራት እንደሚያስፈልግ አመላክቷል ፡፡
ትኩረት ያሻዋል የተባለው የሰብአዊ መብት አጠባበቅ
በጉባዔው ላይ የተገኙት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ወይዘሮ ፋጤ ሴርሞሎ በተለይ ከዜጎች የሰብአዊ መብት አጠባበቅ ጋር ተያይዞ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባ ጠቅሰዋል ፡፡ የፍትህ ሥርዓት አገልግሎት በከተማም ሆነ በገጠር ያለው ማህበረሰብ የአገልግሎቱ ፈላጊ መሆኑን የጠቀሱት አፈ ጉባዔዋ “ ከሰብአዊ መብት አጠባበቅ ጋር ተያይዞ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል ፡፡ አሁን የሚገረፍ አለ ብላችሁ ታምናላችሁ ወይ ? ይህ ትክክል አይደለም ፡፡ በዝርዝር የማነሳው ጉዳዩ በጣም የሚያም በመሆኑ ነው ፡፡ ይህን ለማረምና ለማሻሻል በቅንጅት ለመሥራት የተዋቀረው የፍትህ አካላት ጥምረት ወደ ሥራ መግባት አለበት “ ብለዋል ፡፡
የጉባዔው ተሳታፊዎች ምን አሉ ?
የዳኝነትና የፍትህ ዘርፍ ተቋማት ጥምረት የፖሊስ ፣ የማረሚያ ቤቶች ፣ ፍርድ ቤቶች ፣ የፍትህ አካላት ባለሙያዎችስልጠናና የህግ ምርምር ተቋምን ጨምሮ የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን ያካተተ ነው ፡፡ በጉባዔው ላይ የተሳተፉት የየዘርፉ ተወካዩችም በፍትህ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ይስተዋላሉ ሥላሏቸው ችግሮችና መፍትሄዎቻቸው አስተያየታቸውን ሰጥተዋል ፡፡
ይህቺ ዓለም የምትጠፋው በመጥፎ ሰዎች ክፋት ሳይሆን በጥሩ ሰዎች ዝምታ ነው በማለት አስተያየታቸውን የጀመሩት አንድ የጉባዔው ተሳታፊ “ ዞሮ ዞሮ ይህን ማነው የሚፈጽመው ካልን ሰው ነው የሚፈጽመው ፡፡ ምርመራዎችና መዝገቦች ላይ ብልሽት እንዳለ አየተናል ፡፡ ከሙስና ጋር በተያያዘ የንጽህና ችግር አለ ፡፡ ይህን መቅረፍ ይገባናል ብለን ማስመር አለብን “ ብለዋል ፡፡
ተጠያቂነት እንዲኖር
እያንዳንዱ የፍትህ ተቋም የየራሱ ተልዕኮ ቢኖረውም በጥምረትና በመናበብ መሥራት እንደሚገባ የጠቆሙት የክልሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ወይዘሮ ፋጤ ሴርሞሎ “ በተለይ የተጠያቂነት አሠራር ሊኖር ይገባል ፡፡ የፍትህ ተቋማቱ ቀልጣፋ፣ፈጣንና ዘመናዊ የፍትህ ስርዓትን በመዘርጋት ለዜጎች ህገ መንግስታዊ መብቶችና ነፃነት እንዲከበር በቁርጠኝነት መሥራት ያሥፈልጋል ። በፍትህ የተገልጋዩን የእርካታ ደረጃ ለማሳደግ ችግር ፈቺ ቅንጅታዊ አሰራሮችን የበለጠ ማጠናከር ያስፈልጋል “ ብለዋል ፡፡ በጉባዔው መጨረሻ በክልሉ የዳኝነትና የፍትህ ዘርፍ ተቋማት ጥምረት አባል መሥሪያቤቶች በቅንጅት ለመሥራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል ፡፡
ሸዋንግዛው ወጋየሁ
ሸዋንግዛው ወጋየሁ
ኂሩት መለሰ
ታምራት ዲንሳ