ኤርሚያስ
እሑድ፣ መጋቢት 16 2010ኤሌክትሪካል ኢንጂነሪግ አጠኑ።የኮምፒዉተር ሳይንቲስት፤ መምሕረም ሆኑ-ተባባሪ ፕሮፈሰር።ደግሞ እንደ ስነ-ፅሑፍ አፍቃሪ ሰወስተኛ ልቦለድ መፅሐፋቸዉን በቀደም አሳታሙ።
ዶክተር ኢንጂነር ደራሲ ዋልተንጉስ ዳርጌ።ሁለት ተቃራኒ መስክን ያጣመሩ ምሁር።የዛሬ እንግዳችን ናቸዉ።ዶክተር ዋልተንጉስ።
ሁለቱን አጣመሩት።ቋንቋቸዉም ቢያንስ ሰወስትን ያሰባጠረ ነዉ።ነገሌ ቦረና ተወልዱ፤ ደሴ፤ ናዝሬት እያሉ አደጉ።ተማሩ።በአማርኛ ችሎታቸዉ አይጠረጠሩም።ናዝሬት ዩኒቨርስቲ-አጠኑ።ደብረዝይት አስተማሩ።የእንግሊዝኛ ቋንቋ ችሎታቸዉ ዳበረ ብለን ብንገምት አንሳሳትም።እስከ PHD የደረሰ ትምሕርታቸዉን በሁለት የጀርመን ዩኒቨርስቲዎች አጠናቀቁ።ከሁለቱ ዩኒቨርስቲዎች ባንዱ Technische Universität Dresden እያስተማሩ ጀርመን ይኖራሉ።ጀርመንኛ ቻሉ ማለት ነዉ።
የሚፅፉት ግን ባደጉበት አማርኛ፤ በሚኖሩበት ጀርመንኛም አይደለም።በተማሩበት እንግሊዝኛ እንጂ።ሁለት ምክንያት አላቸዉ።
ከዚሕ ቀደም The Eunuch and the kings Daughter እና The reason for life ያሏቸዉን ሁለት መፀሐፍት አሳትመዋል።ሰወስተኛዉ ኤርሚያስ ነዉ።399 ገፅ አለዉ።ባለፈዉ የካቲት ታተመ።የመፅሐፉ ስም የተሰየመበት ኤርሚያስ ድንገት ሳይታሰብ ናይሮቢ ተሰነፀ፤ ኢትዮጵያ ተወለደ።የልጅነት ዘመኑን እዚያዉ ኢትዮጵያ ኖረ።ከዚያ ወደ ጀርመን ተሻገረ።እናቱ ወደ ትምሕርት-ጥናት ምርምሩ፤ አባት ወደ ንግድ-ሐብቱ ያዘነብላሉ።ኤርሚያስ በወጣትነት ዘመኑ ባለትዳር ሴት እስከማፍቀር ከጅሎትም ነበር።
ደራሲዉ፤ ቀለም የቀመሱ ኢትዮጵያዉን ለትምሕርት በተለይም ለከፍተኛ ትምሕርት ያላቸዉን ጉጉት፤ የሚጓጉለትን ትምሕርት ከዉጪ ሐገር ለማግኘት የሚከፍሉትን መስዋዕትነት ኮለል እያለ በሚፈስ ቋንቋ እና ስልት ደራሲዉ እየተረከ የሚጠይቀዉን እንድንጠይቅ ይጓጉጠናል።በርግጥ ለከፍተኛ ትምሕርት ያን ያሕል መስዋዕትነት መክፈል አስፈላጊ ነዉ?
ሙሉዉን ታሪክ ያንብቡት።ዶክተር ዋልተንጉስ ባልትዳር ናቸዉ።የሁለት ልጆች አባት።
ስማቸዉም የሰወስት ቃላት ቅይጥ ነዉ።ዋል፤ ከ ወይም ተ ንጉስ።ከንጉስ ጋር እንዲዉሉ ወላጆቻቸዉ ተመኙላቸዉ።ጀርመን ንጉስ የለም።ከማጋር ይዉሉ ይሆን?ላምሲ የተሰኘዉ የአሜሪካ አሳታሚ ድርጅት ያሳተመዉ ኤርሚያስ መፅሐፍ በመላዉ ዓለም በየመፅሐፍት መደብሩ ይገኛል።ዶክተር፤ ኢንጂነር ደራሲ ዋልተንጉስ ዳርጌን አመሰግናለሁ።ነጋሽ መሐመድ ነኝ መልካም ምሽት።
ነጋሽ መሐመድ
ኂሩት መለሰ