ምሥራቅ አሜሪካ በበረዶ ተውጧል
እሑድ፣ ጥር 15 2008ማስታወቂያ
በዩናይትድ ስቴትስ ከበረዶ ውሽንፍሩ ጋር ተያይዞ የመጣው የክረምት አውሎ ንፋስ፤ ከፍሎሪዳ እስከ ኒውኤንግላንድ ዘልቋል። በ10 ሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የኤሌክትሪክ አገልግሎት ሲቋረጥባቸው፤ ከ8,400 በላይ የአየር በረራዎች በበረዶው ምክንያት ተሰርዘዋል። ኒው ዮርክ፣ ዋሽንግተን ዲሲ እና አካባቢዎቿ ዛሬም ጸጥ እረጭ እንዳሉ ነው። ፍቃድ ከተሰጣቸው ተሽከርካሪዎች በስተቀር በኒው ዮርክ መኪና መንዳት የተከለከለ ሲሆን፤ በዋሽንግተን ዲሲ ደግሞ የመንገድ ትራንስፖርት አገልግሎቶች ተቋርጠዋል። በአብዛኞቹ ግዛቶች ዛሬም የአየር ንብረት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንደጸና ይገኛል። ይኽ የበረዶ ውሽንፍር በዩናይትድ ስቴትስ ከበርካታ ዓመታት ወዲህ እጅግ ብርቱ እንደሆነ ተነግሮታል። መንገዶች ላይ በተፈጠረው የበረዶ ግግር ቢያንስ 6 ሰዎች የመኪና መንሸራተት አደጋ ተከስቶባቸው መሞታቸው ተዘግቧል። በርካታ ሰዎች ቀደም ባሉት ቀናት መጠጦችና መባልዕት ገዝተው ቤታቸው ማኖራቸው ተጠቅሷል። በፊላዴልፊያ፣ ኒውዮርክ እና ዋሽንግተን ከተሞችን ጨምሮ በ10 የዩናይትድ ስቴትስ ግዛቶች የአየር ንብረት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ታውጇል።
ልደት አበበ
ማንተጋፍቶት ስለሺ