ሩሲያ በሰሜናዊ ዩክሬን ሱሚ ከተማ ላይ በፈጸመችው ጥቃት በትንሹ 31 ሰዎች ተገደሉ
እሑድ፣ ሚያዝያ 5 2017
ሩሲያ በሰሜናዊ ዩክሬን በምትገኘው ሱሚ የተባለች ከተማ ላይ በባልስቲክ ሚሳይል ዛሬ እሁድ ጠዋት በፈጸመችው ጥቃት በትንሹ 31 ሰዎች መገደላቸውን ዩክሬን አስታወቀች። ከሟቾቹ መካከል ሁለት ሕጻናት ይገኙበታል። አስር ሕጻናትን ጨምሮ ሌሎች 84 ሰዎች በጥቃቱ ጉዳት እንደደረሰባቸው ዩክሬን ገልጻለች።
ሱሚ ከሩሲያ ድንበር አቅራቢያ የምትገኝ እና በተደጋጋሚ ኃይለኛ ጥቃት የተፈጸመባት ከተማ እንደሆነች የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ዘግቧል።
በሁለት ሚሳይሎች ሳይፈጸም አልቀረም በተባለው ጥቃት ሕንጻዎች ነጉደዋል፤ ዛፎች ተገንድሰዋል። አውቶቡስ እና ተሽከርካሪዎች ጋይተዋል።
ሩሲያ የሱሚ ማዕከላዊ ክፍልን የመታችው ሰዎች የሆሳዕና በዓልን ለማክበር ወደ ቤተክርስቲያን በሚሔዱበት ዕለት መሆኑን የገለጹት ፕሬዝደንት ቮሎዶሚር ዜሌንስኪ በቴሌግራም ባስተላለፉት መልዕክት ዓለም ጫና ሊያደርግ እንደሚገባው አሳስበዋል።
ዜሌንስኪ “ዩናይትድ ስቴትስ፣ አውሮፓ እና በዓለም ላይ ይህ ጦርነት እና ግድያ እንዲያበቃ የሚፈልግ ሁሉ ሩሲያ የምትሻው እንዲህ አይነት ሽብር ነው። ጦርነቱን እያራዘመች ትገኛለች። በጠብ ጫሪው ላይ ጫና ሳይደረግ ሰላም አይመጣም” ሲሉ ጽፈዋል።
ጥቃቱ የተፈጸመው የአሜሪካ ልዑክ ስቲቭ ዊትኮፍ ከፕሬዝደንት ቭላድሚር ፑቲን ተገናኝተው በተወያዩ በሁለተኛው ቀን ነው። የሩሲያ እና የዩክሬን ጦርነት ለማቆም አሜሪካ የምታደርገው ግፊት አካል የሆነው የባለፈው ዓርብ ውይይት “ውጤታማ” እንደነበር የሩሲያ ልዩ ልዑክ ኪሪል ዲሚትሪቭ ተናግረው ነበር።
ዜሌንስኪ ግን ከሩሲያ ጋር የሚደረጉ “ንግግሮች ተወንጫፊ ሚሳይሎችን እና ከአየር የሚወረወሩ ቦምቦችን አላቆሙም” ብለዋል። “ሩሲያን በተመለከተ የሚያስፈልገው ለሽብርተኛ የሚገባው አቋም መሆን” እንዳለበት ዜሌንስኪ ጥሪ አስተላልፈዋል።
የፈረንሳይ ፕሬዝደንት ኤማኑዌል ማክሮ ዛሬ የተፈጸመው ጥቃት በሩሲያ ላይ በኃይል የተኩስ አቁም መጫን እንደሚያስፈልግ ጠቋሚ መሆኑን ገልጸዋል።
“ሩሲያ ብቻ ይህን ጦርነት እንደምትፈልግ ሁሉም ያውቀዋል። ለሰው ሕይወት፣ ለዓለም አቀፍ ሕግ እና ለፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ባላት ንቀት ዛሬ ሩሲያ ጦርነቱ እንዲቀጥል እንደምትሻ ግልጽ ሆኗል” ሲሉ ማክሮ ኮንነዋል።