1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሩዋንዳና የኮንጎ አማፅያን

ዓርብ፣ ሐምሌ 19 2005

ምሥራቅ ኮንጎ ውስጥ ለሸመቁት አማፅያን የውጭ ኃይሎች የሚሰጡትን ድጋፍ እንዲያቆሙ ዩናይትድ ስቴትስ ጠየቀች ። የዩናይትድ ስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ ትናንት ለተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት ባሰሙት ንግግር ሁሉም ወገኖች ለኮንጎ አማጽያን የሚሰጡትን ድጋፍ በአስቿኳይ እንዲያቆሙ ጠይቀዋል ።

የፀጥታው ምክር ቤት ባወጣው መግለጫም መንግሥታት በኮንጎ ዲሞክራሲያዊት ሪፐብሊክ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ከመግባት እንዲቆጠቡና በተመድ ሸምጋይነት 11 የአካባቢው አገራት ለፈረሙት የሰላም ስምምነት ድጋፍ እንዲሰጡ አሳስቧል ። የዩናይትድ ስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ ትናንት የተባበሩት መንግሥትት ድርጅት የፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት በታላላቅ ኃይቆች አካባቢ ጉዳይ ላይ በመከረበት ውይይት መንግሥትት የኮንጎ ለዩጋንዳ አማፅያንን ከመደገፍ እንዲቆጠቡ የአገር ስም ሳይጠቅሱ በጥቅሉ ነበር ያሳሰቡት ። ይሁንና መልዕክታቸው ለሩዋንዳ እልፍ ሲልም መሆኑ ግልፅ ነበር ። ምክር ቤቱ በጉዳዩ ላይ ከመነጋገሩ ካንድ ቀን አስቀድሞ የአሜሪካን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጄን ፕሳኪ በተለይ ሩዋንዳ M23 ለተሰኘው የኮንጎ አማፂ ቡድን የምትሰጠውን ድጋፍ በአስቸኳይ እንድታቆምና ወታደሮቿንም ከምሥራቅ ኮንጎ እንድታስወጣ ጥሬ አስተላልፈው ነበር ።

የM23 አማጽያንምስል AP

ቃል አቀባይዋ የሩዋንዳ ወታደራዊ ባለሥልጣናት ለአማፂው ቡድን ድጋፍ እንደሚሰጡም መረጃዎች መኖራቸውን አስታውቀው ነበር ። አሜሪካን መረጃ የምትለው የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ሂዩመን ራይትስ ዋች በቅርቡ ስለሩዋንዳ ያወጣውን ዘገባ ነው ። የሂዩመን ራይትስ ዋች አጥኚ ካሪና ቴርትሳኪን ሩዋንዳ ለአማፂው ለM23 የምትሰጠውን ድጋፍ ይዘረዝራሉ ።

« ሩዋንዳ የምትሰጠው ድጋፍ የተለያየ ቅርፅ አለው ። ለምሳሌ የታጠቁና የደንብ ልብስ የለበሱ ወታደሮች ከሩዋንዳ ወደ ኮንጎ ድንበር አቋርጠው በተደጋጋሚ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ አንዱ ነው ። ኮንጎ ለሚገኘው ለ M 23 የጦር መሣሪያዎችን ጥይቶችንና ምግብ ማቅረብን ያካትታል ። ከM23 ጋር የሚዋጉ ወጣት ወንዶችን ከሩዋንዳ መመልመልንና በመጨረሻም የሩዋንዳ ወታደራዊ መኮንኖች በኮንጎ ድንበር ላይ በተካሄደ የአዳዲስ የ M 23 ምልምሎች ሥልጠና ላይ መሳተፈቸውንም ይጨምራል ።»

ሂዩመን ራይትስ ዋች መረጃውን የሰበሰበው የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማነጋገር ነው ። አንዳንዶቹም መረጃ በመስጠታቸው ለደህንነታቸው የሚሰጉ ሰዎች ነበሩ

ጆን ኬሪምስል Reuters

« በርካታ የዓይን ምስክሮችን አነጋግረናል ። ከመጋቢት እስከ ሐምሌ ድረስ ከ 100 በላይ ቃለ መጠይቆችን አድርገናል ። ያነጋገርነውም በተለያየ ደረጃ ላይ የሚገኙ ሰዎችን ነው ። ከመካከላቸው M 23ን ከድተው የወጡ የቀድሞ ተዋጊዎች ይገኙበታል ። ቃላቸውን በመስጠት ህይወታቸውን ለአአደጋ ያጋለጡ ሰላማዊ ሰዎችንም አነጋግረናል ። »ሩዋንዳ M23ን ትደግፋለች የሚለው ክስሲቀርብባት የአሁኑ የመጀመሪያ አይደለም ። ባለፈው ሰኔ የተባበሩት መንግሥታት የአጥኝዎች ቡድን ሩዋንዳ በጎረቤቷ ኮንጎ ጉዳይ ጣልቃ እንደምትገባ የሚያመለክት ዘገባ አቅርበውነበር።ሩዋንዳ ግን M23 ንትደግፋለችየሚለውን ክስ አትቀበልም ። የኮንጎ አጎራባችና የአካባቢው ሃገራት በጎረቤት አገር የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ላለመግባትና ለታጣቂ ቡድኖች ድጋፍ ላለመስጠት ተስማምተዋል ። ይሁንና ጣልቃ ገብነቱ አልቆመም ምክንያቱን በአገሮች መካከል የሚካሄዱ ግጭቶችን በማጥናት መፍትሄውን የሚጠቁመው የክራይስስ ግሩፕ ባልደረባ ማርል አንድሬ ያስረዳሉ ።

የኮንጎና የሩዋንዳ ፕሬዝዳንቶችምስል dapd

« ምሥራቅ ኮንጎ ውስጥ የምትገኘዋ ሰሜን ኪቩ አለመረጋጋትዋ ለሩዋንዳና ለዩጋንዳ ቀጥተኛ ጥቅም አለው ። እንደሚታወቀው የኮንጎ ማዕድንን ለውጭ ንግድ ለማቅረብ አካባቢው ከግጭት ነፃ እንዲሆን ጥረቶች እየተደረጉ ነው ። በሰሜን ኪቩ ግጭቱ የቆመ እለት ኮንጎ ማዕድኖቿን በብዛት ለውጭ ገበያ ማቅረብ ትችላለች ። ይህ ደግሞ በሩዋንዳ ኤኮኖሚ ላይ ከበድ ያለ ቀጥተኛ ተፅእኖ ያሳድራል ። በዩጋንዳ ላይም ያነሰም ቢሆን ተፅእኖ ይኖረዋል። »

ሩዋንዳ የኮንጎውን አማፂ M23ን ትደግፋለች በሚለው ዘገባ ምክንያት ዓለም ዓቀፍ ማዕቀብ ተጥሎባታል ። የጀርመን መንግሥትም ሩዋንዳ በኮንጎ ስለ ምትፈፅመው ጣልቃ ገብነት የወጣውን ዘገባ እንደሚያውቅ እየተባባሰ የሄደው ግጭትም እንደሚያሳስበው አስታውቋል ። የጀርመን የልማት ትብብር ሚኒስትር ከአንድ ወር በፊት እንዳስታወቁት እጎአ በ2014 ጀርመን ለሩዋንዳ በጀት ድጋፍ መስጠት መቀጠል አለመቀጠሏ የሚወሰነው ምስራቅ አፍሪቃዊቱ ሐገር በኮንጎው ግጭት ገንቢ ድርሻ የምትጫወት ከሆነ ነው ።

ሂሩት መለሰ

አርያም ተክሌ

.

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW