ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቼስኮስ በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ተዘከሩ
ቅዳሜ፣ ሚያዝያ 18 2017
የሮማ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ሊቀጳጳስ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ፍራንቼስኮስ ሥርዓተ ቀብር መሥዋዕተ ቅዳሴ በቅድስት መንበር ቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ በተካሄደበት በዛሬው እለት የመታሰቢያና ስርዓተጸሎት አዲስ አበባ ውስጥ በሚገኘው በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የልደታ ማሪያም ካቶሊካዊት ካቴድራል ቤተክርስቲያን ተደርጓል።
እግዚአብሔር አምላክ የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስን ነፍስ በመንግስቱ እንዲቀበል በተደረገው የዛሬው የቤተክርስቲያንቷ የፀሎትና የፍትሃት መርሃግብር ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀስላሴ ዓለም ትልቅ ሰው አጥታለች ሲሉ ሀዘናቸውን ገልጸዋል።
የሮማ ካቶሊካዊት ቤተክርስትያን ሊቀ-ጳጳስ ፍራንሲስ የቀብር ሥነ-ሥርዓት ተፈጸመ።
ርዕሰብሔር ታዬ በዚህን ወቅት እንዳሉት ፖፕ ፍራንሲስ ከአመታት በፊት ኢትዮጵያ እና ኤርትራ መካከል እርቅ መውረዱ ሲነገር ከማንም ቀድመው ደስታቸውን የገለጹና ለሰላም የተጉ አባት ነበሩ ብለውአቸዋል፡፡
“የመጀመሪያውን ታላቅ የበረከት ድምጽ ያሰሙ እሳቸው ነበሩ” ያሉት ርዕሰ ብሔሩ “ዓለም በከፋበትና ሁሉም ክፉ በሚናገርበት ጊዜ እሳቸው ኢትዮጵያ እና ኤርትራ መካከል ሰላም ስወርድ የሰላም ንፋስ በአፍሪካ ይነፍሳል” ማለታቸውና በደቡብ ሱዳን ተፋላሚዎች መካከልም የነበረው ጠብ እንዲቋጭ ወድቀው ተንበርክከው መማጸናቸውን አስታውሰዋል፡፡ ቀን ለጠመመባቸው ሁሉ ጸሎት በማድረግም የሚታወቁ በማለት ዓለም በሳቸው ህልፈት ታላቅ ሰው ማጣቷን ገልጸዋልም፡፡
ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ በተካሄደው በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የልደታ ማሪያም ካቶሊክ ካቴድራል ቤተክርስቲያን የተገኙ የሃይማኖቱ ተከታይ ምዕመናን እና አባቶች ልዩ ልዩ ጸሎትና መታሰቢያ በማድረግ ታድመዋል፡፡
የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ ሕይወት እና የቤተክርስትያኒቱ መጻዒ ጊዜ
በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ረዳት ጳጳስ አቡነ ተስፋስላሴ ተስፋዬ ታደሰ እንደተናገሩት ርዕሰ ሊቃነጳጳሳት አቡኔ ፍራንቼስኮስ በመንፈሳዊ አይን በተስፋ ጊዜ ያለፉ ብለውአቸዋል፡፡
“ጊዜው የትንሳኤ ሰሞን እንደመሆኑ የተስፋ ጊዜ ነውና ነፍሳውን መንግስተሰማያት እንዲያወርስልን እለምናለሁ” ያሉት አቤኔ ተስፋስላሴ፤ ፖፕ ፍራንሲስን በተለያዩ የአገልግሎት እርከኖች ለእግዚአብሔር ያደሩ ብለውአቸዋል፡፡ አቤኔ ፍራንቼስኮስ ለደሃ የሚደርሱ ለዓለም ሰላምም አብዝተው የፀለዩ ጥሩና ርሁሩ አባት ብለዋቸዋል፡፡
በመርሃግበሩም የአቡኔ ፍራንቼስኮ (ፖፕ ፍራንሲስ) ከልጅነት እስከ ከ1.4 ቢሊየን በላይ ተከታይ ያላት የዓለማቀፋዊት ቤተክርስቲያን መሪነት የደረሱበት የህይወት ታሪካቸው ተወስቷል፡፡ ከሳቸው መማር የሚገባም ይህ ነው ሲሉ አቡኔ ተስፋ ስላሴ አስረድተዋል፡፡
“እኛ እንደ ቤተክርስቲያን ከሳቸው የምንማረው ነገር ክርስቶስን መከተል ማለት በህይወት መመስከር፣ አገልግሎት መስጠትና ወንድማማችነትን መስበክ ነው” በማለትም በተስፋ መቁረጥ ውስጥ እንኳ ቢሆን በእግዚአብሔር ድጋፍ ተስፋ ማድረግን ማስተማራቸውን አብራርተዋል፡፡
የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስን ስንብት
ባሳለፍነው ሰኞ ሚያዚያ 13 ቀን 2017 ዓ.ም. በ88 ዓመት እድሜያቸው ከዚህ ዓለም ያለፉት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቼስኮስ (ፖፕ ፍራንሲስ) ላለፉት 12 ዓመታት የሮማ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ሊቀጳጳስ በመሆን ማገልገላቸው በህይወት ታሪካቸው ተጠቅሷል፡፡
ሥዩም ጌቱ
እሸቴ በቀለ