ሳልቫ ኪር የሰላም ስምምነት ፈረሙ
ረቡዕ፣ ነሐሴ 20 2007የደቡብ ሱዳን ፕሬዝዳንት ሳላቫ ኪር 20 ወር የዘለቀውን የሱዳን የርስ በርስ ጦርነት ለማስቆም ያስችላል የተባለውን የሰላም ስምምነት ዛሬ ጁባ ደቡብ ሱዳን ውስጥ ፈረሙ። የሰላም ስምምነቱ የተፈረመው የደቡብ ሱዳንን መንግሥትና አማፅያንን ሲሸመግሉ የከረሙት የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ፣ የዩጋንዳው ፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒና የኬንያው ፕሬዝዳንት ኡኹሩ ኬንይታ በተገኙበት ነው። ኪር ስምምነቱን ከመፈረማቸው በፊት ለአካባቢው አገራት መሪዎች ባሰሙት ንግግር የማይቀበሏቸው ብዙ ነጥቦች ቢኖሩትም ስምምነቱን እንፈርማለን ብለዋል። የአማፅያኑ መሪና የቀድሞው የደቡብ ሱዳን ምክትል ፕሬዝዳንት ሪክ ማቻር የሰላም ውሉን ባለፈው ማክሰኞ አዲስ አበባ ውስጥ ፈርመዋል። በውሉ መሠረት ማቻር ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንት ይሆናሉ ተብሎ ይጠበቃል። ኪር አለኝ ያሉትን ስጋት በዝርዝር ያሰፈሩበትን ሰነድ ለሸምጋዮቹ አስረክበዋል። ስጋቶቻቸውም የጁባ ከጦር እንቅስቃሴ ነፃ መሆንዋ እና በፖሊሲ ጉዳዮች ላይ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንቱን እንዲያማክሩ የሚያሳስቡ ቅድመ ሁኔታዎች ናቸው። ኪር የሰላም ስምምነት በፈረሙበት በዛሬው እለት አማፅያን ከጁባ በስተደቡብ የምትገኝ አንዲት ከተማን መያዛቸውን አስታውቀዋል። አማፅያኑ እንዳሉት ከተማይቱን የያዙት ወታደሮቻቸው ጥቃት ከደረሰባቸው በኋላ ነው። በሌሎች አካባቢዎችም ከመንግሥት ኃይሎች ጋር ውጊያ እየተካሄደ መሆኑንም ተናግረዋል ።
ኂሩት መለሰ
ነጋሽ መሐመድ