ቅርስን መጠበቅ ማንነትን መጠበቅ
ዓርብ፣ ጥቅምት 14 2012«ስሜ ሲራክ አስፋዉ ይባላል፤ ላለፈዉ 41 ዓመታት ሆላንድ ሃገር ነዋሪ ነኝ፤ እኔ ባላሰብኩትና በማላዉቀዉ ሁኔታ በኢትዮጵያ አቆጣጠር በ 1990 ዓ.ም ይህ በአፄ ፋሲለደስ ዘመነ መንግሥት የነበረ ቅርስ ሆላንድ ዉስጥ እጄላይ ወደቀ። » ይላሉ በሆላንድ ነዋሪ የሆኑት ኢትዮጵያዊ፤ መስከረም 21 ከማለዳ ጀምሮ የዓለም የብዙኃን መገናኛ ቀልብ ስቦ የዋለዉ ፤ በአንድ ግለሰብ ለ 21 ዓመታት ተደብቆ የቆየዉ በ1626ዓ.ም በአጼ ፋሲለደስ ዘመነ መንግሥት የተሠራ ዘውድ፤ ወደ ሃገሩ ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ ዝግጅት ላይ መሆኑ የመሰማቱ ዜና ነዉ። በኔዘርላንድ ለ41 ዓመት የኖሩት አቶ ሲራክ አስፋው በአሁኑ ጊዜ በኔዘርካንድ በአስተዳደር አማካሪነት ይሰራሉ ።
በሆላንድ፤ ሮተርዳም ነዋሪ የሆኑት አቶ ሲራክ እንደገለፁት፤ ለ 21 ዓመታት ደብቀዉና ጠብቀዉ ያቆዩት የኢትዮጵያ ጥንታዊ የነገሥታት ዘዉድ፤ ኢየሱስ ክርስቶስ እና አሥራ ሁለቱ ሐዋርያት የተቀረጹበት ሲሆን፤ ቤታቸው በእንግድነት የመጣ ሰው ትቶት ከሄደው ሻንጣ ውስጥ እንዳገኙት ነዉ የተናገሩት። ዘውዱን እንዳዩትም የተሰረቀ መሆኑን በማሰብ፣ ኢትዮጵያ እስካልተመለሰ ድረስ ከቤታቸው እንደማይወጣ ፣ ማንነታቸውን ይፋ ላላደረጉት ዘውዱ ለተገኘበት ሻንጣ ባለቤት መናገራቸውን፤ ይህ ዉብና እጅግ ጥንታዊ የኢትዮጵያ ነገስታት ዘዉድ በአሁኑ ጊዜ ደህንነቱ በተጠበቀ ስፍራ እንደሚገኝ ነዉ የገለፁት ቅርስነቱ የኢትዮጵያዉያን ነዉ ከኢትዮጵያ መዉጣት የለበትም ብለዋል። በኔዘርላንድ ለ 41 ዓመታት የኖሩት አቶ ሲራክ አስፋዉ፤ በአሁኑ ጊዜ በአስተዳደር አማካሪነት እየሰሩ ይገኛሉ።
« በእኔ እምነት ቅርስነቱ ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ስለሆነ ከኢትዮጵያ የለበትም አልነበረበትም ቅርስ ማጣት ታሪክ ማጥፋት መሆኑን ፤ ብሎም የነገስቶቻችን ታሪክ እና ቅርስ የኢትዮጵያ መሰረቶች መሆናቸዉን አጥብቄ ስለማዉቅና ስለማምን ፤ ወድያዉኑ ሚያዝያ 17 ቀን፤ 1990 ዓ.ም፤ የሚከተለዉን ጥሪ በጊዜዉ በነበረ ድረ-ገጽ ፤ የሃሳብ እና የመፍትሄ ትብብር፤ እና ምን ይደረግ በማለት ፤ ለኢትዮጵያዉያኑ ወገኖቼ ጥያቄ አቀረብኩ። »
ከዝያም ነዉ ከአዉሮጳ አፍሪቃ መካከለኛዉ ምስራቅ እስያና አሜሪካ የሚገኙ 44 የዓለም ሃገራት የብዙኃን መገናኛዎች እንዲሁም ከ 150 በላይ ጋዜጦች በጉዳዩ የዘገቡት። አቶ ሲራክ በመጀመርያ ለኔዘርላን ብሎም ለታወቁ የዓለም መገናኛ ዘዴዎች ላይ ቀርበዉ ይህን ጥንታዊ ቅርስ መመለስ እንደሚፈልጉ ከማስታወቃቸዉ በፊት በሃገር ቤት የቅርስ ጉዳይ ያገባቸዋል ካልዋቸዉ ሰዎች ጋር ተነጋግረዋል።
ሙሉ ቃለ-ምልልሱን የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን ይከታተሉ።
አዜብ ታደሰ
ተስፋለም ወልደየስ