በሀዋሳ የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል የሚደረግ ጥረት
ማክሰኞ፣ ጥር 21 2011በርካታ የአካባቢ ጥበቃ ተቆርቋሪዎች እንደሚስማሙት የፕላስቲክ ውጤቶች ከኒውከለር ቦንብ ባልተናነስ የምድራች ትልቅ ሥጋት በመሆን ላይ ይገኛሉ ብለው ያምናሉ። በኢትዮጲያ ያለውን የምጣኔ ሀብት መነቃቃት ተከትሎ ፕላስቲክን ለተለያዩ ምርቶች መያዣና ማሸጊያነት የመጠቀሙ ልምድ እየጨመረ መምጣቱ አገሪቱን የዚህ ሥጋት ተጋሪ እንድትሆን አድረጓታል ። ከፌደራሉ ንግድና እንዱስትሪ ሚንስቴር የተገኘው መረጃ እንደሚያመለከትው በአሁኑወቅት በኢትዮጲያ ከስልሳ በላይ የታሸጉ ውሃዎችን የሚያመርቱ ፋብሪካዎች በሥራ ላይ ይገኛሉ። ጥቅልና ብትን የምርት ማሸጊያ ፕላስቲኮችን የሚያመርቱ ፋብሪካዎች ቁጥርም ከዚህ እንደማይተናነስ ነው የሚገመተው። ትልቁ ችግር ታዲያ የፕላስቲክ ውጤቶቹ ማምረቱ ላይ ሳይሆን ከአገልግሎት በኋላ የሚወገዱበት መንገድ የአካባቢ ብክለት አያሰከተለ መገኘቱ ላይ ነው ። በፕላስቲክ ብክለት ተጋለጭነት ከተጋረጠባቸው ከተሞች አንዷ የሆነችው ሀዋሳ ችግሩን አስቀድሞ ለመከላከል የሚያስችሉ ተግባራት ማከናወን ከጀመረች ዓመታትን አስቆጥራለች። በከተማዋ በተደራጁ ማህበራት አማካኝነት የፕላስቲክ ውጤቶች ዳግም ጥቅም ላይ የሚውሉበት አሠራር ገቢራዊ እየሆነ ይገኛል ። በዚሁ ተግባር ላይ ከተሠማሩት ማህበራት መካካል ደግሞ የአባ ኮዳ የቆሻሻ አስወጋጅና መልሶ መጠቀም ማህበር ይገኝበታል። የማህበሩ ሰብሳቢ አቶ ዘውዴ አበበ በማህበሩ የሥራ አንቅስቃሴ ዙሪያ ተከታዩን ገልጸውልኛል። የአባ ኮዳ የቆሻሻ አስወጋጅና መልሶ መጠቀም ማህበር ከከተማዋ የሚሰበስባቸውን የፕላስቲክ ውጤቶች መልሰው ወደሚጠቀሙ ፍብሪካዎች በማቅረብ ብቻ የተወሰነ አንዳልሆነ ሰብሳቢው አቶ ዘውዴ ይናገራሉ። ይልቁንም የተለያዩ የመገልገያ ቁሳቁሶችን በማምረትና ቆሻሻን ወደ ገንዘብ በመቀየር ለአረንጓዴ ልማት የራሳቸውን አስተዋጽኦ በማበረከት ላይ አንደሚገኙ ነው ሰብሳቢው የሚያስረዱት። በአባ ኮዳ የቆሻሻ አስወጋጅና መልሶ መጠቀም ማህበር ከተማዋን ከቆሻሻ ብክለት ከመታደጉ በተጨማሪ /ለከተማው ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፈጠር መቻሉ በራሱ ጥቅሙን ባለብዙዘርፈ አድርጎታል ማለት ይቻላል። በሀዋሳ ከተማ ዳራቻ ላይ በሚገኘው የማህበሩ የቆሻሻ ማከማቻና መለያ ቅጥር ግቢ ውስጥ በሥራ ላይ ያገኘኋቸው ወጣቶችም የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ነግረውናል። የደቡብ ክልል አካባቢ ፤ ደንና የአየር ንብረት ለውጥ ቁጥጥር ባለስልጣን በሀዋሳ ከተማ ቆሻሻን መልሶ በጥቅም ላይ ለማዋል የተጀመረው እንቅስቃሴ ውጤቶች እየታዩበት ነዉ።
ባለፈው የ2010 በጀት ዓመት ብቻ ከፍተኛ መጠን ያላቸው የፕላስቲክ ውጤቶችን መልሶ በጥቅም ላይ በማዋል ከተማዋን ከብክለት ለመከላከል መቻሉን ነው የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሳሙኤል የሚናገሩት። አንደ አቶ ሳሙዔል ገልጻ አሁን በሀዋሳ ከተማ የተጀመረውን ፕሮጀክት በቀጣይ ወደ ሌሎች ከተሞች ለማስፋፋት በክልል አካባቢ ፤ ደንና የአየር ንብረት ለውጥ ቁጥጥር ባለስልጣን አማካኝነት የአዋጭነት ጥናት በመካሄድ ላይ ይገኛል። ጥናቱ ሲጠናቀቅ በክልሉ አባዛኞቹ ከተሞች የቆሻሻ ውጤቶችን መልሶ በጥቅም ላይ በማዋል የአካባቢ ብክልትን የመከላከሉ ስራ በስፋት አንደሚቀጥል ነው ዋና ዳይሬክተሩ ያመላከቱት። ሙሉ ዝግጅeune የችምጽ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን ይከታተሉ።
አዜብ ታደሰ
ሸዋንግዛዉ ወጋየሁ