በሆለታው ችሎት ስለተፈጸመው ግድያ በቦታው ከነበሩ የተጎጂ ጠበቃ አንደበት
ዓርብ፣ ግንቦት 28 2018
በምዕራብ ሸዋ ዞን ወልመራ ወረዳ ሆለታ ከተማ በችሎት ላይ የተገደሉት ዳኛ ስርዓተ ቀብር ዛሬ ተፈጽሟል፡፡ ትናንት ሓሙስ ግንቦት 27 ቀን 2018 ዓ.ም. በሆለታ ከተማ በባልና ሚስት መካከል ለአንድ ዓመት ገደማ ሲካሄድ የነበረውን የፍርድ ቤት ሂደት በማስቻል ላይ የነበሩት ዳኛ እና ከሳሽ በዚያው በችሎት ላይ ሳሉ ነበር በተከሳሽ በጥይት ተደብድበው የተገደሉት፡፡
በዚህን ወቅት በችሎቱ ላይ የነበሩት የከሳሽ ጠበቃ የሆነውን ለዶቼ ቬለ ሲናገሩ፤ ተከሳሽ የፍርዱን አፈጻጸም ትዕዘዝ ካደመጡ በኋላ ባለቤታቸውን እና የእለቱን ተረኛ ዳኛ በጥይት ተኩሰው መግደላቸውን ገልጸዋል፡፡
ጠበቃ ተስፋዬ መገርሳ እንደ ወትሮው ስራቸው ላይ በጠዋቱ ተሰይመዋል፡፡ ትናንት ሓሙስ ግንቦት 27 ቀን 2018 ዓ.ም. ግን ያጋጠማቸው እጅግ አስደንጋጭ እና በህይወታቸው ተመልክተውት የማያውቁት፤ ደግሞም መቼም ሊረሱት የማይችሉት ነገር ነው፡፡ እንደወትሮው በጥብቅና ስራቸው ችሎት ፊት ቆመው በሚከራከሩበት ወቅት በፍርዱ ፊት በተቃራኒያቸው ከቆመው ተከሳሽ የተኩስ እሩምታ በደንበኛቸው እና በፍርድ መንበር ላይ በተቀመጡት ዳኛ ላይ ሲዘንብ በአይናቸው ሲመለከቱ፤ "ቀኔ ስላልነበር እንጂ እኔም የጥቃቱ ዒላማ ነበርኩ” የሚል አስተያየት እንዲሰጡ አስገደዳቸው፡፡
የባልና ሚስት ንብረት ክፍፍል ላይ ከሁለት ሳምንታት በፊት ውሳኔ ያገኘው መዝገብ ላይ በተሰየመው ችሎት ሲጀመር ነገሮች በተለመደው ሰላማዊ መንገድ ሲካሄድ ነበር ሲሉ አስተያየታቸውን ለዶይቼ ቬለ የሰጡ በቦታው ላይ የነበሩ የአይን እማኝ ጠበቃ፤ የውሳኔው አፈጻጸም ላይ የእለቱ ተረኛ ዳኛ የ አስተያየታቸውን የቀጠሉት ጠበቃ ተስፋዬ፤ የባልና ሚስቱ ክርክሩም ለአንድ ዓመት ያህል የቆዬ እንደነበር ነው ያመለከቱትሰጡትን ትዕዛዝ ካደመጡ በኋላ ተከሳሽ ሽጉጣቸውን መዘዋል ብለዋል፡፡ "ከሁለት ሳምንት በፊት ንብረታቸውን እንዲካፈሉ ተወስኖ ነበር” ሲሉ፡፡
በችሎቱ ላይ የተፈጸመው ግድያው እንዴት ተከሰተ?
በዚያው ችሎት ላይ የነበሩ የአይን እማኙ ጠበቃ እንዳሉት፤ "በትናትናው እለት ድርሻዋ እንዲሰጣት ጠይቀን ስለነበር እሱም ገዳይ (ተከሳሽ) አቶ አቅናው በቀለ በችሎቱ ቀርበው ነበር”፡፡ አሁን ባለቤታቸው (ሟች) ወ/ሮ አልማዝ ጋብቻቸው በፍርድ ቤቱ ሂደት በመፍረሱ የንብረት ክፍፍልም እንዲደረግላቸው አፈጻጸም ላይ የተሰየመም ችሎት ነበር ፣የትናንቱ ችሎት ብለዋል፡፡
"ከሳሽና ተከሳሽ አብረው ያፈሩት በርካታ ንበረትም ነበራቸው” ያሉት ጠበቃው በባንክ የታገደ ገንዘብን ጨምሮ በስማቸው የነበሩ በርካታ መኖሪያ ቤቶች በውሳኔው መሰረት እኩል እንዲካፈሉ ለባንክ እና ለመሬት አስተዳደር እንዲፈጽሙ ችሎቱ ትዕዛዝ አስተላልፎ ቀጠሮ ላይ ሲደርስም ነው ይህ ክስተት የተከሰተው ብለዋል፡፡ "የሟች ጠበቃ ሆኜ ቀጠሮ እየተጠባበቅኩኝ ነው ችሎት ላይ ተኩስ የሰማሁት” ያሉት ጠበቃው፤ "ሟች ተተኩሶባት አጠገበ ስትወድቅ እኔም በድንጋጤ ወድቄ ነበር” ሲሉ በሰዓቱን የሆነውን ክስተት አስረድተዋል፡፡ ቀጥሎም አሉ ጠበቃው፤ "በዚህ መሃል ጉዳዩን በማስቻል ላይ የነበሩ ተረኛ ዳኛ ወርቄ ፈከንሳ በድንጋጤ ስትጮኽ ተከሳሹ ጥቃት አድራሽ ቀጣይ ተኩስ ለማድረግ እያቀባበለ ነበር” ነው ያሉት፡፡ ታዲያ በዚህን ጊዜ በድንጋጤ ከችሎቱ ክፍል ሮጠው የወጡት ጠበቃ ተጨማሪ የመሳሪያ ድምጽ ሲሰሙ፤ በችሎት መንበሩ ላይ የነበሩ ዳኛ በጥይት ሲደበደቡ ነበር፡፡ "ዳኛዋ ስትጮኅ ተከሳሹ ጥይት እያቀባበለ ወደእሷ ሲዞር ነው በድንጋጤና በሩጫ ከዚያ ወጣሁት”ብለዋል የአይን እማኙ ጠበቃ፡፡
ሲያሟግት የቆዩ የቤተሰብ ክርክር
ዳኛዋ ስራቸውን ከመስራት ውጪ የፈጸሙት በደል አልነበረም ያሉት ጠበቃው፤ ለአንድ አመት ግድም በክርክር ላይ የነበረው የባልና ሚስት ጉዳይ ላይ የግራ ቀኝ ክርክር፣ ሚስክር ማስረጃን ከተለያዩ አቅጣጫዎች ሲያዩ ቆይተው መዝገቡን አገላብጠው ነው ውሳኔ የሰጡት ሲሉ አድካሚውን የፍርድ ሂደት ገልጸውታል፡፡
በሃብት ክፍፍል ሙግት ላይ የነበሩት የቀድሞ ባልና ሚስት ጋብቻቸውን በፍርድ ቤት አፍርሰው አሁን ላይ በተለያዩ ቤቶች እየኖሩ የነበሩ መሆኑንም አክለው የገለጹት የከሳሽ ጠበቃው፤ በርካታ ቤተሰብ አብረው ያፈሩ ትልልቅ ሰዎች እንደነበሩም ገልጸዋል፡፡ "ትልልቅ ሰዎች ናቸው፤ የመጨረሻ ልጃቸው እንኳ ወደ 17 አመት እድሜ ላይ መድረሱን ከደንበኛዬ ሰምቻለሁ” ብለዋል፡፡ ከስምንት ያላነሰ ልጆች ያፈራ ትልቅ ቤተሰብ እንደነበሩም እንደሚያውቁ ጠቁመዋል፡፡
"ባላመልጥ የሟቾቹ እጣ ይደርሰኝ ነበር” ጠበቃ
በትናንቱ የፍርድ ሂደት ችሎቱን የሰየሙ መቿ ዳኛ ብቻ እንደነበሩ እና በዚያን ችሎት ላይም ከሁለቱ ባለጉዳዩች እና ዳኛ እና ጠበቃው ውጪ ማንም በችሎት አዳራሹ ውስጥ እንዳልነበርም ነው ጠበቃው የገለጹት፡፡ "እኔን ፈጣሪ ቢያተርፈኝም ከሳሽ ደንበኛዬ እና ዳኛዋ ተጎድተው ሆስፒታል ከደረሱ በኋላ ህይወታቸው አልፏል” ነው ያሉት፡፡
ጥቃት አድራሹም ተከሳሽ በራሱም ላይ ጉዳት ማድረሱን የገለጹት ጠበቃው፤ አሁን ላይ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው በህክምና ላይ እንዳሉ መስማታቸውንም ጠቁመዋል፡፡ ፍርድ ቤቶች ውስጥ ችሎት ሲሰየም በሕጉ መሰረት ባለጉዳዮች ተፈትሸው ወደ ችሎት መግባት ይኖርባቸው ነበር ያሉት ጠበቃው፤ ነገር ግን እንዲህ ያለ መዘናጋት በብዙ ፍርድ ቤቶች የተለመደ ሆኖ እንደሚመለከቱት ገልጸዋል፡፡ ከዳኛዋ በላይ የተከሳሹ ዒላማ እንደነበሩ የሚጠረረጥሩት ጠበቃው፤ እሮጠው ባይወጡ እሳቸውንም የሚጠብቃቸው ተመሳሳይ እጣ ሊሆን እንደሚችል በምክንያታዊነት ገምተዋል፡፡
የድርጊቱ መወገዝ
ስለጉዳዩ ተጨማሪ መረጃን ለመጠየቅ ለወልመራ ወረዳ ፍርድ ቤት ኃላፊ አቶ ስርኔሳ ኩመላ ደውለን በቀብር ላይ መሆናቸውን ተናግረው ማብራሪያ ግን አልሰጡንም፡፡
በጉዳዩ ላይ በይፋዊ የማህበራዊ ገጹ ላይ መግለጫ ያወጣው የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ግን ተከሳሽ ባደረሱት ጥቃት በወልመራ ወረዳ ፍርድ ቤት የባልና ሚስት ችሎት በመዳኘት ላይ የነበሩት ዳኛ ወርቄ ፈካንሳን መግደላቸውን ገልጿል፡፡ ጥቃት አድራሹ ተከሳሽ ባለቤቱ የነበሩትን ወ/ሮ አልማዝ መኮንንም በሽጉጥ ተኩሰው እንደገደላቸው እንዲሁም በራሱም ላይ ጉዳት አድረሶ አሁን በህክምና ላይ መሆኑን ገልጿል፡፡
በአሁኑ ወቅት በተጨማሪም በወንጀሉ የተጠረጠሩ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለዋል ያለው ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የተከሰተውን ድርጊት በምንም መንገድ ተቀባይነት የሌሌው ሲል አውግዞታል፡፡
ስዩም ጌቱ
ኂሩት መለሰ
ፀሐይ ጫኔ