በሆርሙዝ ወሽመጥ ለመርከቦች እንቅስቃሴ ደኅንነት ትራምፕ ለአጋሮቻቸው ያቀረቡት ጥሪና አውሮጳ
ሰኞ፣ መጋቢት 7 2018
የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሆርሙዝ ወሽመጥ የዓለም የንግድ መርከቦች እንቅስቃሴ ደኅንነት እንዲጠበቅ ከአጋሮቻቸው የትብብር እርዳታ ጠይቀዋል። ብሪታንያና ፈረንሳይን ጨምሮ ቻይና ጃፓን እና ደቡብ ኮሪያ የእርዳታ ጥሪ ከቀረበላቸው ሀገሮች ውስጥ ይገኙበታል። የሆርሙዝ ወሽመጥ ክፍት ሆኖ እንዲቀጥል ፍላጎቱ መሆኑን ያስታወቀው የአውሮጳ ኅብረት ዛሬ በጉዳዩ ላይ ብራሰልስ ውስጥ ተነጋግሯል። 27ቱ የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ዛሬ ስብሰባ ከማካሄዳቸው በፊት የኅብረቱ የውጭ ጉዳዮች ሃላፊ ካያ ካላስ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ችግሩን ለመፍታት ፣ማደረግ የሚችሉት ላይ እንደሚነጋገሩ ገልጸዋል።
የካቲት 21 ቀን 2018 ዓ.ም. እሥራኤልና ዩናይትድ ስቴትስ በጋራ በኢራን ላይ የከፈቱት ጦርነት እና የኢራን የአጸፋ ጥቃት በዓለም ዙሪያ የነዳጅ ዋጋን አንሯል። የንግድ መርከቦችን ጉዞ ያሳልጥ የነበረው የሆርሙዝ ሰርጥ፣ኢራን በዚያ የሚያልፉ መርከቦች ላይ ጥቃት እንደምትሰነዝር በመዛቷ ምክንያት በዚያ ይተላለፉ የነበሩ የባህረ ሰላጤው አገራት ነዳጅ ሆነ ሌሎች ምርቶችና ሸቀጦችን የጫኑ በርካታ መርከቦች ወይ ባሉበት ቆመዋል አለያም በደቡባዊ አፍሪቃ በኩል ያለውን ረዥሙን የጉዞ መስመር መጠቀም ግድ ሆኖባቸዋል።
ፈረንሳይ ሁኔታዎች የሚፈቅዱ ከሆነ በወሽመጡ የሚተላለፉ መርከቦችን የማጀብ ዓለም አቀፍ ተልዕኮ ለማሳካት እየተንቀሳቀሰች መሆኑን አስታውቃለች። በዚህ ተልዕኮ ኔዘርላንድስ ጣልያን እና ግሪክ በዚህ ተልኮ የመሳተፍ ፍላጎት እንዳለቸው ፤ ስፔይንም በሆነ መንገድ ልትሳተፍ እንደምትችል አንድ ስማቸው ያልተጠቀሰ አንድ የፈረንሳይ ከፍተኛ ባለሥልጣን ተናግረዋል። ጀርመን በበኩልዋ ዩናይትድ ስቴትስ እና እሥራኤል በኢራን ላይ ስለሚካሂዱት ጦርነት ግልጽ መረጃ እንደምትፈልግ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ ተናግረዋል። በዚህ ጉዳይ ላይ ከብራሰልሱ ዘጋቢያችን ገበያው ንጌሴ ጋር የተደረገው ቃለ ምልልስ ከታችባለው የድምጽ ማዕቀፍ ላይ ይገኛል።
ገበያው ንጉሴ
ኂሩት መለሰ