በምስራቅ ወለጋ ስለተገደሉ የአማራ ተወላጆች የዐይን ምስክሮች እና መንግስት ምን አሉ?
ረቡዕ፣ ነሐሴ 19 2013ማስታወቂያ
በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን ኪረም ወረዳ በርካታ ንፁሃን ዜጎች በታጣቂው ኦነግ ሸኔ መገደላቸውን የዓይን እማኞች ለዶይቼ ቬለ ተናገሩ። የዓይን እማኞቹ ድርጊቱ የተፈፀመው ሟቾቹ ራሳቸውን መከላከል በማይችሉበት ሁኔታ ሲሆን አሁን ድረስ የት እንደገቡ ያልታወቁ መኖራቸውንና ይህንን ጥቃት ለሸሹ ሰዎችም የደረሰላቸው እንደሌለ ገልፀዋል። ሕፃናትን ጨምሮ አቅመ ደካሞች እንደተገደሉ፣ ሴቶችም መደፈራቸውንና ቤታቸው ላይም እሳት እንደተለቀቀበትም ተናግረዋል። እናት ፓርቲ ትናንት ባወጣው መግለጫ 231 ስምና አድራሻቸው የታወቀ ንፁሃን ዜጎች በታቀደና በተጠና አካሄድ ፍጅት ተፈፅሞባቸዋል ብሏል። ይህ ድርጊት ተሸፋፍኖና ተደቦድበስብሶ እንዲያልፍ እየተደረገ ነው ያለው እናት ፓርቲ ወንጀሉንም የዘር ማጥፋት ሲል ገልፆታል።
ድርጊቱ ኦነግ ሸኔ በተባለው ቡድን መፈፀሙን የገለፀው የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ቡድኑ አሳቻ ሰዓት ጠብቆ ያደረሰው ጥቃት መሆኑን ተናግሯል። የክልሉ የፀጥታ ኃይል ወደ ሥፍራው መላኩም ተገልጿል።
ሰለሞን ሙጬ
ታምራት ዲንሳ
ሸዋዬ ለገሰ