በሠራተኞች ላይ ሥጋት ፈጥሮ የነበረው የአደጋ ሥጋት ሕግ ማሻሻያ ተደረገበት
ዓርብ፣ ግንቦት 29 2017
የኢትዮጵያ መንግሥት "ማንኛውም የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ" የተባሉ አደጋዎች በዜጎች ላይ እንዳይደርሱ የመከላከልና አደጋው ሲደርስም "ለተጎጂዎች የሰብዓዊ ድጋፍ በጊዜ እንዲደርስ የማድረግ ሕገ- መንግስታዊ ኃላፊነት ያለበት በመሆኑ" የሰብአዊ ድጋፍን ከውጭ ጥገኝነት በማላቀቅ በራስ አቅም ለመሸፈን ያግዛል የተባለለት አዋጅ ትናንት ተሻሽሎ ፀድቋል።
ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን የገቢ ምንጮች ምንድን ናቸው?
ለዚህ ሥራ ማስኬጃ የሀገር ውስጥ ሀብት ማሰባሰቢያ ስልት በሚል ከተያዙት ውስጥ "ባንኮችና አነስተኛና ጥቃቅን የፋይናንስ ድርጅቶች ከሚሰጡት የብድር መጠን ላይ፣ የዲጂታል ባንኪንግ አገልግሎት ተጠቃሚዎች ከሚከፍሉት የአገልግሎት ክፍያ ላይ፣ የኢንሹራንስ ኩባንያዎች ለሚሰጡት አገልግሎት ከሚሰበስቡት የፕሪሚየም ክፍያ ላይ የሚታሰብ፣ ከማንኛውም የአክስዮን ዲቪደንድ ድርሻ፣ ከበረራ ትኬት ሽያጭ፣ የቴሌኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት የሚሰጡ ድርጅቶች ለድምጽና ዳታ አገልግሎት ከሚያስከፍሉት የአየር ሰዓት ዋጋ ላይ፣ ከፓስፖርትና ቪዛ አገልግሎት ክፍያ፣ ነዳጅ ሽያጭ አቅራቢ ድርጅት ከሚያገኘው ገቢ ላይ፣ ማንኛውም የንግድ ፈቃድ በሚወጣበት እና በሚታደስበት ጊዜ በቁርጥ የሚታሰብ የሚሉት ይገኙበታል ።
በረቂቁ ላይ "የመንግሥት እና የግል ድርጅት ተቀጣሪ ሰራተኞች ከሚከፈላቸው የተጣራ ደመወዝ ላይ የሚታሰብ" ተብሎ ተጠቅሶ የነበረውና ሥጋት ፈጥሮ የነበረው ይህ የገቢ ምንጭ ግን እንዲነሳ ተደርጓል።
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነት እና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ዶክተር ፈቲህ ማህዲ የዚህን ምክንያት ገልፀዋል። "የተጣራ ደሞዝ ላይ የሚቆረጥ መዋጮ ሠራተኞች ላይ ተደራራቢ የወጪ ጫና እንዳያሳድር ነው"።
የኢትዮጵያ ሠራተኞች ማህበራት ኮንፌደሬሽን ማሻሻያውን ደግፏል
በኑሮ ውድነት ምክንያት ደሞዝ ተከፋዩ ሠራተኛ ኑሮን መቋቋም ተስኖት በከፍተ ችግር ውስጥ ይገኛል ያሉት የኢትዮጵያሠራተኞች ማህበራት ኮንፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ ይህ ማሻሻ በመደረጉ ጥያቄያችን ውጤት አግኝቷል ብለዋል። ባለ ሁለት ገጽ ማብራሪያ የያዘ ጥያቄ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስገብተው እንደነበር በማስታወስ።
"ሥጋት ላይ ያለ ሰው እንዴት አድርጎ አደጋ ሥጋትን ይከላከላል የሚል [መግለጫ] ስንሰጥ ነበር። ቀርቷል ከተባለ ውጤት አግኝተንበታል ማለት ነው"።
ሥራው የሁሉንም ርብርብ ይጠይቃል - አደጋ ሥጋት አመራር ኮሚሽን
የኢትዮጵያ አደጋ ሥጋት አመራርኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ሥራ አስፈፃሚ ዶክተር ዓለማየሁ ወጫቶ በቅርቡ ለዶቼ ቬለ በሰጡት ማብራሪያ ሰብአዊ ድጋፍ በራስ አቅም ሲባል የሁሉም ዜጋ ኃላፊነት የማይቀር እንደሚሆን ጠቅሰዋል።
"ሰብአዊ ድጋፍ በራስ አቅም የሚለው ንቅናቄ እየተሠራ ነው ያለው። ምክንያቱም ሁልጊዜ የተቀባይ እጅ ከታች ነው። የሰጪ እጅ ከላይ ነው"።
በሌላ በኩል የሚኒስትሮች ምክር ቤት ለፌዴራል መንግሥት መደበኛ ወጪዎች፣ ለካፒታል ወጪዎች፣ ለክልሎች የሚሰጥ ድጋፍ እና ለዘላቂ የልማት ግቦች ማስፈጸሚያ ድጋፍ የሚውል ያለውን "ሁለት ትሪሊዮን [ብር] የሚጠጋ በጀት" ደግፎ ትናንት ወደ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መርቶታል።
ሰሎሞን ሙጬ
ኂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ