በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ የደቡብ ሱዳን ሥደተኞች ጋምቤላ ክልል ገቡ
ቅዳሜ፣ ሐምሌ 5 2017
በደቡብ ሱዳን መንግሥት ጦር በተቃዋሚዎቹ ኃይላት መካከል የሚደረገዉን ዉጊያ የሸሹ በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ የሐገሪቱ ዜጎች ምዕራብ ኢትዮጵያ ጋምቤላ ክልል መግባታቸዉን የክልሉ ባለሥልጣናትና የተባበሩት መንግሥታት የሥደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር (UNHCR) አስታወቁ።የጋምቤላ ክልል ባለሥልጣናት እንዳሉት ካለፈዉ መጋቢት ጀምሮ ኢትዮጵያ የገቡት የደቡብ ሱዳን ሥደተኞች ቁጥር 50 ሺሕ ይደርሳል።ከዚሕ ቀደም ከደቡብ ሱዳን የተፈናቀሉ ከ380ሺሕ በላይ ሥደተኞች ኢትዮጵያ ዉስጥ እንደሠፈሩ ነዉ።
ስደተኞቹ በ”ማታር”ና በ”ሙን” ተጠልለዋል
ካለፈው መጋቢት 2017 ዓም ጀምሮ በደቡብ ሱዳን መንግሥት ጦርና በመንግሥት ተቃዋሚ ኃይሎች መካክል በተፈጠረው ጦርነት ምክንያት በርካቶች ወደ ኢትዮጵያ፣ ጋምቤላ ክልል ዋንታዋ ወርዳ ገብተዋል፣ “ለስደተኞቹ በቂ ምግብ እየቀረበላቸው አይደለም” ያሉት የዋንታዋ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ጋትዊች ቡዝ ህብረተሰቡ ያለውን እያካፈላቸው እየኖሩ ነው ብለዋል፡፡ በእርሳቸው ግምት የተመዘገቡና ያልተመዘገቡ 50ሺህ ያክል ስደተኞች ማታርና ሙን በተባሉ በተባሉ የወረዳው አካባቢዎች ይኖራሉ፡፡
በዋናነት ሴቶችና ህፃናት የሚበዙባቸው ስደተኞች ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ፣ ጋምቤላ ክልል፣ ዋንታዋ ወደታባለው ወረዳ መግባታቸውን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የስደተኞች ኮሚሽን (UNHCR) ለዶይቼ ቬሌ በላከው ደብዳቤ አረጋግጦልናል፡፡ ድርጅቱ በደብዳቤው እንዳሳወቀው ስደተኞቹ በድንገት አካባቢያቸውን በመልቀቃቸው ለምግብ እጥረት፣ ለህክማና እጦት፣ ለመጠለያና ለሌሎች ችግሮች የተጋለጡ እንደሆኑ ገልጧል፡፡
“ከ35ሺህ በላይ አዲስ ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ ገብተዋል” UNHCR
35ሺህ የሚሆኑት ስደተኞች ማታርና ሙን በተባሉ አካባቢዎች በፈራረሱና ባልተጠናቀቁ ቤቶች ለደህንነታቸው ምቹ ባልሆነ መንግድ ተጨናንቀው እንደሚኖሩ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የስደተኞች ኮሚሽን በላከው ደብዳቤ አመልክቷል፡፡
የተለያዩ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት የምግብ፣ የንፁህ መጠጥ ውሀና ሌሎችንም እገዛዎ ያደረጉ ቢሆንም ካለው ችግር አኳያ እገዛው በቂ እንዳልሆነ ነው ድርጅቱ በደብዳቤው ያሳወቀው፡፡
3 ሚሊዮን ዶላር የነብስ አድን ገንዝብ ሰለመመደቡ
በዚህ ሳምንት ማዕከላዊ የአስቸኳይ ጊዜ ምላሽ ፈንድ Central Emergency Response Fund (CERF) 3 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ለደቡብ ሱዳን ሰደተኞች፣ ለነፍስ አድንና ሰደተኞቹ ለሚኖሩባቸው የማህበረሰብ ክፍሎች ጭምር ለጤናና ሌሎች ማህበራዊ አገልግሎት የሚውል ገንዛብ መመደቡን አመልክቷል፡፡
የሰደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት የጋምቤላ ቅርንጫፍ ኃላፊ አቶ መዝገበ ገብረማሪያም በደቡብ ሱዳን በነበረ ጦርነት 35ሺህ የሚገመቱ ስደተኞች በተለያዩ ጊዜዎች ወደ ጋምቤላ ክልል ዋንታዋ ወረዳ መግባታቸውን ገልጠዋል፡፡
“... አጠቃላይ በደቡብ ሱዳን ባለፈው በመንግሥትና በተቃዋሚ ኃይሎች መካክል በላይኛው ናይል ግዛት ናስርና ኡላንግ በተባለው አካባቢ በተፈጠረው ግጭት በርካታ ደቡብ ሱዳናዊያን ቡርቤ ወደሚባል አካባቢ ተፈናቅልው ነበር፣ ግጭቱ ሲያይል ደግሞ ከቡርቤ ተፈናቅለው ሙንና ማታር ላይ ነው ያሉት፡፡” ብለዋል
“ ‘ሏክዶንግ’ በተባለ ቦታ መጠለያ ካምፕ ይገነባል” ስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት
እስካሁን ለተፈናቃዮች መጠለያ ካምፕ እንዳልተገነባ የተናገሩት አቶ መዝገበ፣ አሁን ከጋምቤላ ክልል መንግሥት ለመጠለያ ግንባታ ቦታ “ሏክዶንግ” በተባለ አካባቢ መውሰዳቸውንና የግንባታ ቀደመ ዝግጅቶች እየተደረጉ እንደሆነ ነው አብራርተዋል፡፡
እስክዚያው ድረስ የእርዳታ ስጪ ድርጅቶች አስፈላጊውን እገዛእንዲያደርጉ እየተደረገ መሆኑንም አቶ መዝገበ አስረድተዋል፡፡
ቀደም ሲልም በጋምቤላ ክልል በ7 የመጠለያ ጣቢያዎች ከ380ሺህ በላይ የደቡብ ሱዳን ተፍናቃዮች እንደሚኖሩ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
በአጠቃላይ ከአንድ ሚሊዮን በላይ በዋናንት የሶማሊያ፣ የደቡብ ሱዳንና የኤርትራ ስደተኞች በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች እንደሚኖሩ የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ኮሚሽን ድርጅት (UNHCR) ሪፖርቶች ያሳያሉ፡፡
ዓለምነው መኮንን
ነጋሽ መሐመድ
እሸቴ በቀለ