በአውስትራሊያ በተፈጸመ ጥቃት 12 ሰዎች ተገደሉ
እሑድ፣ ታኅሣሥ 5 2018
በአውስትራሊያ ቦንዲ በተበለ የባሕር ዳርቻ 2 ጠመንጃ የታጠቁ ግለሰቦች ዘመናት ያስቆጠረውን ባሕላዊ ክብረ በዓላቸውን ሲያከብሩ በነበሩ ይሁዲዎች ላይ ዛሬ በፈጸሙት የተኩስ እሩምታ ቢያንስ 12 ሰዎች መሞታቸውን ተሰማ። ከጥቃት ፈጻሚዎቹ አንዱ በፖሊስ ሲገደል ሁለተኛው ደግሞ ቆስሎ በቁጥጥር ሥር ውሏል።
ከ1,000 በላይ የሚሆኑ ይሁዲዎች ቦንዲ በተባለው የባሕር ዳርቻ ተሰባስበው ጥንታዊ ፌስቲቫላቸውን በሚያከብሩበት ሰዓት 2 የታጠቁ ግለሰቦች በታዳሚያኑ ላይ የተኩስ እሩምታ ማዝነባቸውን የአይን እማኞች ለሮይተርስ ተናግረዋል።
በሐገሪቱ ቴሌቪዥንና በማሕበራዊ መገናኛ ብዙሐን የተሰራጩ ተንቀሳቃሽ ምስሎች እንዳመለከቱት አንዱ ታጣቂ በሕዝቡ ላይ ለመተኮስ ሲሰናዳ አንድ ወጣት መሳሪያውን ለማስጣል ሲሞክር ታይቷል። ይሁንና የራሱም ሆነ የሌሎችንም ህይወት ሳይታደግ ቀርቷል።
በጥቃቱ ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ 12 ይሁዲዎች ሲሞቱ 29 ደግሞ ቆስለዋል። ከቆሰሉት መካከል ሁለት የፖሊስ አባላት ይገኙበታል።
የአውስትራልያ ፖሊስ ከአንደኛው ጥቃት አድራሽ መኪና ተቀጣጣይ ፈንጂዎች ማግኘቱን አስታውቋል። ድርጊቱንም «የሽብር ጥቃት» ብሎ የገለጸው ሲሆን ምርመራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አክሏል።
የአውስትራልያ ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኒስ «ዛሬ በቦንዲ የባሕር ዳርቻ የተፈጸመው ክፉ ድርጊት ለማሰብ የሚከብድ ነው» ሲሉ ገልጸውታል። ለሟቾች ቤተሰቦች መጽናናትን በመመኘት።
ድርጊቱን የተለያዩ ሐገራት መሪዎች እያወገዙት ይገኛሉ። የእስራኤል ፕረዚደንት አይዛክ ሄርዞግ «በይሁዲዎች ላይ የተፈጸመ የጭካኔ ጥቃት» በማለት ድርጊቱን አውግዘዋል።
የጀርመን መራሔ መንግስት ኦላፍ ሾልስ በጥቃቱ የተሰማቸውን ጥልቅ ሐዘን ገልጸዋል። የአውሮፓ ሕብረት ኮሚሽን ፕረዚደንት ኦርዙላ ፎን ዴር ላይን በኤክስ ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ድርጊቱን «አስደንጋጭ» ብለውታል።
በይሁዲ ማሕበረሰብ ላይ ያነጣጠረው ጥቃት ያወገዙት ፎን ዴር ላየን ከአውስትራሊያ መንግስት እና ከይሁዲ ማሕበረሰብ እንደሚቆሙም አክለዋል። የፈረንሳይ፣ የእንግሊዝ፣ የዮክሬይን መሪዎችም በየፊናቸው ድርጊቱን አውግዘዋል።