የዓለም ሥራ ድርጅት (ILO) 20ኛ የአፍሪካ ጉባኤ
ቅዳሜ፣ ግንቦት 16 2017
ኢትዮጵያ በዚህ ሳምንቱን በሙሉ ስታስተናግድ የቆየችው የዓለማቀፉ የስራ ድርጅት (ILO) 20ኛ ጉባኤ በየሁለት ዓመታቱ በተለያዩ የአፍሪካ አገራት እየተዘዋወረ የሚደረግ ነው፡፡ አብዛኛዎቹ የአፍሪካ አገራት ተሳታፊ በሆኑበት በአዲስ አበባው ጉባኤም ከ26 በላይ የአገራት ሚኒስትሮች እና ከተለያዩ የዓለም አገራት ደግሞ ከ50 ያላነሱ አገራትን የወከሉ ተሳታፊዎች መታደማቸው ተነግሯል፡፡
በዚህ ጉባኤ የተሰናዳው አዲስ ዲክላሬሽን አንዱ የጉባኤው ስኬት መሆኑን ለመገናኛ ብዙሃን የተናገሩት የከተማና መሰረተ-ልማት ሚኒስትር ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ የስራ እድል ፈጠራ እና ዘላቂነት ያለው የአከባቢ ጥበቃ ጉባኤው በጥልቅ ከመከረባቸው ነጥቦች ዋናው ነው፡፡ “የአዲስ አበባው ዲክላሬሽን የሰው ኃይልን የሚጠቀሙ የልማት አማራጮችን የሚያበረታታ ነው” ያሉት ሚኒስትሯ አፍሪካ የወጣቶች አገር እንደመሆኗ እያንዳንዱ የልማት ስራዎች የስራ እድልን መፍጠር የሚችሉ መሆን እንደሚጠበቅባቸው አስረድተዋል፡፡ የሚሰሩ ስራዎችም ሰው ተኮር መሆን እንደሚኖርባቸውና በከፍተኛ ደረጃ የስራ እድል መፍጠር እንደሚኖርባቸው ይጠበቃልም ነው የተባለው፡፡
የኢትዮጵያ ከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር እና ከዓለማቀፉ የስራ ድርጅት (ILO) ጋር በመተባባር ያሰናዳው ጉባኤው ወደ ሶስት ሺህ ግድም ታዳሚዎችንም አስተናግዷል፡፡ አብዛኞቹ ከውጪ የመጡ በተባለበት በዚህ ጉባኤ ተሳታፊዎች ለአዘጋጅ አገር ለተሳትፎ ከሚከፍሉት የውጪ ምንዛሪ በተጨማሪ በቆይታቸውም የከተማውን የንግዱን ማህበረሰብ የሚያነቃቃ ግብይት መፈጸማቸው በበጎነቱ ታይቷል፡፡
ጉበኤው ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት አዲስ አበባ ውስጥ በጉባኤተኞቹ የተጎበኙ የመሰረተ ልማቶች ግንባታ ከስራ እድል ፈጠራ እና አከባቢ ጥበቃ ጋር ተያይዘው መታየታቸው ተነግሯልም፡፡ “የልማት ስራዎቹ ከአከባቢ ጥበቃና ከስራ እድል ፈጠራ ጋር መታየት እንዳለባቸውና እያንዳንዱ በአፍሪካ ውስጥ የሚፈሱ የፋይናንስ አማራጮችም ጭምር ይህን ግንዛቤ ውስጥ እንዲያስገቡ አቅጣጫ ተቀምቷል” ሲልም ወ/ሮ ጫልቱ አስተያየታቸውን አስቀምጠዋል፡፡
ኢትዮጵያ ውስት እየተከናወነ ባለው የልማት ሞዴልና የስራ እድል ዘለቄታዊነቱ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡን የፖለቲካል ኢኮኖሚ ባለሙያ አቶ ሸዋፈራሁ ሽታሁን ግን በአስተያየታቸው፤ “80 በመቶ የማህበረሰብ ክፍልን ያቀፈው ግብርናን ስናዘምነው ወደ አምራችነት ከዚም ወደ አገልግሎት ዘርፍ እንዲሸጋገር ይጠበቃል” በማለት በኮሪደር ልማት እና መሰል የኢትዮጵያ የልማት ስራዎች ላይ ስለሚፈጠሩ ዘለቄታዊነት ያላቸውና ቴክኖሎጂን ስለሚያሸጋግሩ የስራ እድል ጥርጣሬ አንስተዋል፡፡