በኢትዮጵያ የሃገራዊ መግባቢያ ቋንቋ አስፈላጊነት ተገቢው ትኩረት እንዲሰጠው ተጠየቀ
ቅዳሜ፣ ታኅሣሥ 15 2015
ኢትዮጵያ አሁን ያለችበት አስቸጋሪ የሰላም እጦትና የፖለቲካ ሁኔታ ስርዓታዊና መዋቅራዊ እንደሆነ ሰሞኑን ሃገራዊ የመግባቢያ ቋንቋን አስመልክቶ በተካሄደ የባለሙያዎች ውይይት ላይ ተጠቅሷል።
በከፊልም ቢሆን ወጣት ልጆች ላይ በትምህርት ፖሊሲና አፈጻጸሙ ላይ ባለሙያዎቹ ተሰርቷል ያሉት ብልሹ አካሄድ፣ አሁን ላለው ችግር በምክንያትነት ተጠቅሷል።
ወጣቱ ትውልድ ሊያገኝ ይገባው የነበረውን ትምህርትና ሃገራዊ ማንነት እንዲያገኝ አለመደረጉ፣ አስተዋጽኦ ማድረጉም ተመልክቷል።
በዩናይትድስቴትስ ከፍተኛ የትምህርት ባለሙያ የሆኑት ዶክተር አዳነ ገበያው፣ሃገራዊ የመግባቢያ ቋንቋ ፋይዳን አስመልክቶ ሲናገሩ፣የሚከተለውን ብለዋል።
ዶክተር አዳነ፣ሃገራዊ የመግባቢያ ቋንቋ እንደ አንድ የትምህርት ዓይነት መሰጠቱ፣ከመማር ማስተማር ሙያና ከትምህርት ጥራት አኳያ ያለውን ጠቀሜታም ያስረዳሉ።
አሁን በኢትዮጵያ ከተጀመረው ሃገራዊ ምክክር ኮሚሽን ተግባር አንጻር ከፍተኛ አንደምታ ቢኖረውም፣ትኩረት ተነፍጎት እንደሚታይ አብራርተዋል።
በአዲሱ የሃገሪቱ ስርዓተ ትምህርት፣የሃገሪቱ የስራ ቋንቋ የሆነው ዐማርኛን፣ እንደ አንድ የትምህርት ዓይነት በሃገራዊ መግባቢያ ቋንቋነት እንዲሰጥ አልተደነገገም ያሉት የትምህርት ባለሙያው፣ይህ መስተካከል እንደሚገባውም አመልክተዋል።
ለዚህ ጉዳይ መፍትሔ ለማፈላለግ ይረዳ ዘንድ በሚመሩት ድርጅት ውይይት መካሄዱን የገለጹልን ደግሞ፣የፒፕል ቱ ፒፕል መስራችና ዋና ዳይሬክተር ዶክተር እናውጋው መሐሪ ናቸው።
ኢትዮጵያ የብዙ ቋንቋዎች ባለቤት ብትሆንም፣እሱን የሚያገናኝና ሕዝቡን የሚያስተሳስር ብሔራዊ የመግባቢያ ቋንቋ አስፈላጊነት ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባም ዋና ዳይሬክተሩ አሳስበዋል።
ታሪኩ ኃይሉ
እሸቴ በቀለ