የሰሜን አሜሪካ ሊቃነ ጳጳሳት ጥሪ
ዓርብ፣ መስከረም 7 2014ዩናይትድስቴትስ በኢትዮጵያ ላይ የያዘችው አቋም አሳስቦናል ሲሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሰሜን አሜሪካ አስር ሊቃነ ጳጳሳት አመለከቱ። ሊቃነ ጳጳሳቱ ለአሜሪካ መንግስት ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንተኒ ብሊንከን እና ሌሎች ባለስልጣናት በፃፉት ደብዳቤ ዩናይትድስቴትስ የኢትዮጵያን ነባራዊ ሁኔታ አስመልክቶ ይዘዋለች ያሉት አቋም ስጋት ያሳደረባቸው መሆኑን ገልፀዋል።በአሜሪካና በካናዳ የሚገኙ የ11 አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት ትናንት ከአሜሪካ ሕዝብ እንደራሴዎችና አማካሪዎቻቸው ጋር ዋሽንግተን ዲሲ ውስጥ በጉዳዩ ላይ ተወያይተዋል።ሊቃነ ጳጳሳቱን ወክለው የኒውዮርክና አካባቢው ሃገረ ስብከት ሊቃነጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ለዶይቸ ቨለ በሰጡት መግለጫ በትናንቱ ውይይት በጎ ምላሽ መገኘቱን ተናግረዋል።
የደሕንነት እና ፍትኅ ለትግራይ ምክትል ፕሬዝደንት ፕሮፈሰር ሙሉጌታ ገብረእግዚዓብሔር በበኩላቸው "የአሜሪካ መንግሥት አቋም ግልጽ ነው። እኛም እንደግፈዋለን።" ሲሉ ተናግረዋል። ፕሮፈሰር ሙሉጌታ ለዶይቼ ቬለ "አንዱ የአሜሪካ መንግሥት እያለ ያለው ነጻ የሆነ ዓለም አቀፍ አካል ምርመራውን ያካሒደው ነው የሚለው። በዚህ ላይ ደግሞ የመንገዶች መዘጋት፣ የሰብዓዊ ዕርዳታ እንዳይገባ መከልከል፣ የመብራት መጥፋት፣ የስልክ መጥፋት፣ የቴሌኮምዩንኬሽን አውታሮች መዘጋጋት እንዲነሳ ነው ጥሪ እያቀረቡ ያሉት" ብለዋል።
ታሪኩ ኃይሉ
ኂሩት መለሰ
እሸቴ በቀለ