1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

በኤርታሌ አዳዲስ እሳተ ጎሞራ መከሰቱ፤ አደገኛ ንጥረነገር አስከትሏል

ኢሳያስ ገላው
ሐሙስ፣ ሐምሌ 10 2017

የኤርታሌ እሳተ ገሞራ በአዲስ መልክ መፈንዳቱን የአፋር ክልል ባህል ቱሪዝም ቢሮ አስታወቀ ከፍተኛ መርዛማ ኬሚካል ያለዉ እና ለሰዉ ልጂ ጤና አስጊ ነዉ ተብሎል እንስሳቶችና ሰዎችም ከአካባቢዉ እንዲርቁ ተመክራል።

Visual Story | Äthiopien Dallol
ከዚህ ቀደም በምሽት የተከሰተው የኤርታሌ እሳተ ገሞራ ፎቶ ከማኅደርምስል፦ Gilles Barbier/picture alliance

በኤርታሌ አዳዲስ እሳተ ጎሞራ

This browser does not support the audio element.

 

በአፋር ክልል ከትናንት በስተያ ጀምሮ ከዋናው ኤርታሌ እሳተ ገሞራ 15 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ አራት ቦታዎች አዳዲስ የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ መከሰቱን የአፋር ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ አስታወቀ።እስከ ዛሬ ከተከሰቱት ፍንዳታዎች የተለየ ነው የተባለው ክስተቱ መሬት መንቀጥቀጥ ያስከተ ነበር ሲሉ አቶ አብዱ አህመድ የአፋር ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የፕሮሞሽን ዳይሬክቶሬት ይናገራሉ። 

የተከሰተው የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ ከእስከዛሬዉ የተለየ ነዉ

«ኤርታሌ የሚታወቅበት ዋናው ቦታ ላይ ግን ከዚህ ቀደም ከነበረው ለይት ይላል፡፡ ተደጋጋሚ የመሬት መንቀጥቀጥ ስሜት ነበረው። ከዚያ ውጭም 2 ቦታዎች ላይ ፈንድቷል፤ በጣም እየሰፋ ሲሄድ ተራራውን እየደረመሰ ነው። አዳዲስ የወጡትንም ቮልካኖ በጣም ከፍተኛ የሆነ ላባ ሆኖ ፈሷል።›› 

ከፍተኛ የሆነ ጭስ የነበረው የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ በአካባቢው ለመተንፈስ አስቸጋሪ የነበረ መርዛማ ጭስ ሲያወጣ እንደነበርም ነው በስፍራው ተገኝተው የተመለከቱት አቶ አብዱ አህመድ የሚናገሩት።

«ጭሱ በጣም ያፍን ነበር፤ አሁን መጥፎ ከሆነ ጋዝ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል፤ ጭሱ ሰው ወዳለበት ሳይሆን ከቀይ ባሕር አለያም ከሰሜን የሚመጣው ንፋስ ቶሎ ጭሱን እየበተነው ነው።»

ፍንዳታው የመሬት መንቀጥቀጥ አስከትሎል

ከዚህ ቀደም የቀለጠ አለት ከጉድጓድ ውስጥ እየወጣ የሚፈስበት እና ብዙፍንዳታዎች የማይታዩበት መሆኑን የሚናገሩት በታላቁ ኢትዮጵያ አስጎብኝ ማሕበር ፕሬዝዳንት እና ጂኦሎጂስት የሆኑት አቶ እንቁ ሙሉጌታ ይህንን የኤርታሌን ፍንዳታ ዓለም ያልጠበቀው እና በአካባቢውም አዲስ ክስተት ነው ይላሉ። 

«አሁን የተከሰተው በጣም ፍንዳታ ያለው ወደ ሰማይ የሚረጭ የቀለጠ አለት ድንጋይ ሳይሆን የሚወጣው አመዱ ነው። በዚህ ላይ ጋዝም ይኖረዋል። በጣም ሀይለኛ የሆነ ጋዝ አለው።»

በኤርታሌ በጎርጎሪዮሳዊው 2009 ዓ,ም የተቀነሰቀሰው እሳተ ጎሞራ ፎቶ ከማኅደርምስል፦ Loic Poidevin/Nature Picture Library/IMAGO

ፍንዳታዉ መርዛማ ጭስ አለው

መርዛማ የሆነ ጋዝና አሲድም በፍንዳታው ወቅት ወደ አየር ተቀላቅሏል የሚሉት አቶ እንቁ ሙሉጌታ በፍንዳታው ጊዜ ወደ ሰማይ የወጣው ጭስ በሰው ልጅ ጤና ላይ እክል ሊያስከትል የሚችል መሆኑን ይገልፃሉ።

«ጋዙ በጣም መርዛማ ነው፤ ከጋዙ ይልቅ የሚጎዳው አመዱ ነው፤ ገና መውጣቱ ነው የአሲድ መጠኑ ከፍተኛ ነው፤ ልክ እንደወጣ የሚገጥም አዲስ የሆነ አሲድ ነው፤ በሰማይ ላይ ብዙ ጊዜ ይቆያል አመድ ስለሆነ በአንዴ አይወርድም። እሱን ከተነፈስክ የደቀቀ ብርጭቆ ወደ ሳንባ እንዳስገባህ ነው የሚቆጠረው።»

በጤና ላይ እክል የሚፈጥር አሲድ አለው

በኤርታሌ የእሳተ ገሞራ ስፍራና በዙሪያው የተፈጠሩ አዳዲስ ፍንዳታዎች ወደ አየር የሚለቁት ጋዝ በሰው ልጅ እና እንስሳዎች ላይ አደጋ ሊያስከትል የሚችሉ በመሆናቸው አስፈላጊው ጥንቃቄ ሊወሰድ እንደሚገባም ጂኦሎጂስቱ አቶ እንቁ ሙሉጌታ ያሳስባሉ።

«አጥኒ ቡድን አካባቢውን ለይቶ የሰውን ልጅ እና እንስሳ እንዳይቀርቡ በማድረግ በአካባቢው የሚጠጣ ውሃ ካለም በመከልከል በአፋር ግመሎች አሉ፤ ቅጠላ ቅጠል የሚበሉ እዚያው በኤርታሌ አካባቢ ነው የሚመገቡት፤ ከተመገቡ በኋላ ቆይቶም ቢሆን ለሞት ይዳርጋቸዋል እና እነሱን መከላከልም ያስፈልጋል።»

ኢሳያስ ገላው

ሸዋዬ ለገሠ

ማንተጋፍቶት ስለሺ

 

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW