በደቡብ ኢትዮጵያ ጅንካ ከተማ ተከሰተ የተባለው አዲሱ በሽታ ማርበርግ ቫይረስ መሆኑ ተገለፀ።
ቅዳሜ፣ ኅዳር 6 2018
ባለፈው ኅዳር 3 ቀን 2018 ዓ.ም. የፌደራል ጤና ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በጋራ ባወጡት መግለጫበደቡብ ኢትዮጵያ «ምንነቱ በመረጋገጥ ላይ ያለ የሔሞራጂክ ፊቨር» በሽታ መከሰቱን አስታውቀው ነበር።ምርመራውን ካካሄዱ በኋላ አርብ ኅዳር 5 ቀን 2018 ዓ.ም.የኢትዮጵያ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ በደቡብ ኢትዮጵያ በጂንካ ከተማ ተከስቶ የነበረው ምንነቱ ያልታወቀ ሲባል የነበረው በሽታ ማርበርግ ቫይረስ መሆኑን አስታውቋል።ያም ሆኖ በአሁኑ ወቅት የበሽታውን ምልክት ያሳየ ወይም በተዋህሲው የተጠረጠረ ሰው እንዳልተገኘ እና በሽታውን የመከላከል እንዲሁም የመቆጣጠር ሥራ እየተሠራ መሆኑን ጠቅሷል። ከሳምንት በፊት በጅንካ ከተማ የተከሰተው ይህ በሽታ ሁለት የጤና ባለሙያዎችን ጨምሮ ስድስት ሰዎችን መሞታቸውን ዶቼቬለ ከአካባቢው ያገኘው መረጃ ያሳያል።
የማርበርግ ቫይረስ በከፍተኛ ሁኔታ ተላላፊ በሽታ ሲሆን፣ እንደ ዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት መረጃ በሽታው ከኢቦላ ጋር ተመሳሳይነት አለው። ምልክቶቹም ትኩሳት፣ድካም፣ የጡንቻ ህመም፣ ተቅማጥ፣ ማስታወክ እና አንዳንዴም ከፍተኛ የደም መፍሰስ በማስከተል ለሞት የሚያበቃ አጣዳፊ በሽታ ነው።ድርጅቱ ትናንት ባወጣው መግለጫ እነዚህ ምልክቶች የታዩበት ሰው በአፋጣኝ ለጤና ተቋማት እንዲያሳውቅ አሳስቧል።ድርጅቱ በበሽታው ክስተት እና ባደረሰው ጉዳት ላይ ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ ከኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት እና ከክልላዊ ጤና ባለስልጣናት ጋር በቅርበት እየሰራ መሆኑን ገልጾ ነበር።
በዚህም፤ የበሽታውን መንስኤ ለማወቅ እና ተጨማሪ ስርጭት እንዳይኖር ለመከላከል የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ የመጀመሪያ ደረጃ ምላሽ ሰጪ ቡድን በማሰማራት የህክምና ቁሳቁሶችን እያቀረበ መሆኑን አመልክቷል።
እስካሁን ድረስ ስምንት በበሽታው ተይዘዋል ተብሎ የተጠረጠሩ ሰዎች ተገኝተዋል፤ያለው የድርጅቱ መግለጫ፤ መንስኤውን በትክክል ለማወቅ በኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የቤተሙከራ ምርመራ እየተካሄደ ነው ማለቱም ይታወሳል።
ፀሀይ ጫኔ
እሸቴ በቀለ