በጅማ ዞን የቡና ማሳ ግጭት የሰው ህይወት ቀጠፈ
ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 17 2010በኦሮሚያ ክልል በጅማ ዞን በማና ወረደ በኬንቴሪ ቀበሌ ለቡና እንስትመንት መሬት የወሰዱ ባለሃብቶችና በአከባብዊ አርሶ አደሮች መካከል ዉዝግብ ከተነሳ ቆይቷል።ለቆየዉ ዉዝግብ መንስቄ የሆነዉ ባለሃብቶቹ ከተሰጠቸዉ የኢንቨስትመንት መሬት በማስፋፋት የሌሎች ገበሬዎችን ማሳ በማያዛቸዉ መሆኑን የዓይን እማኞች ተናግረዋል።
ገበሬዎቹም ተወሰደብን የሚሉት መሬት እንዲመለስላቸዉ በሕግ ቢጠይቁም መልስ እንዳላገኙ የዓይን እማኞቹ ጨምሮ ይናግራሉ። «በሕግ መንገድ መልስ ሳያገኙ ሲቀሩ የኢንቨስትመንት ባለሃብቱ ያጠረበትን አጥር ትላንት ወደ ማሳዉ በመሔድ ማፍረስ ጀመሩ። ባለሃብቱም የማሳዉን ጠበቃ ሰዎች ወደ ማሳዉ ከቀረቡ እንዲገላቸዉ አዝዘዋል። እሱን ተከትሎ በዛሬዉ እለት ሰዎች ለተቃዉሞ ወጥተዋል። ወደ ማሳዉም በመሄድ የባለሃብቱን ንብረት እያጠቁ ይገኛሉ። መንግስት እስካሁን ያለዉ ነገር የለም ግን ፖሊሶች በቦታዉ ይገኛሉ።»
ከጅማ ከተማ በግምት 30 ኪሜ ርቀት ላይ የምትገኘዉ ኬንቴሪ ቀበሌ ዉስጥ በሕገወጥ መሬታችን ወሰደዋል ያሉት ግለሰቦችና የማሳዉ ባለሃብቶች መካከል የተፈጠረዉን ግጭት የዞኑ የኮሚዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ገመቹ ናጋሳ አረጋግጠዋል። ግጭቱ እና አሁን ያለዉን ሁኔታ እንዲህ ሲሉ ይናገራሉ፣ «አሁን መረጃ እንዳለን ከሆነ፣ 10 የሚሆኑ ወጣቶች ባለሃብቱ (ድንበር አልፈዉ) መሬታችንን ይዘዋል በሚል ቅሬታ በተለያየ ጊዜ ሲካሰሱ ነበረ። በዚህ መካሰስ በተነሳም ጉዳዩ ወደአልተፈለገ ሁኔታ እንዳይለወጥና ጉዳዩን እንዲመለከቱ ፖሊስ ወደ ቦታዉ ተልኮ ነበር። የተላኩት ፖሊሶች ወደ ተላኩት ቦታ ሳይደርሱ ወጣቶቹ የቡና ኢንቨስትመንት ያለበት ቦታ ሄደዋል። እዛም ወጣቶቹ ከጥበቃዉ ጋር ተጋጭተዋል። በዚህም ምክንያት አንድ ሰዉ ሞቷዋል። አሁን ባለን መረጃም በጥበቃ ላይ የነበረ ግለሰብም እንደተመታ ነዉ። እሱም በሕይወት መኖር አለመኖሩን እያጣራን እንገኛለን።»
በዚህ ዓመት ከወጣቶችና ከኢንቨስትመንት ጋር የተያያዘ ስራ ዞናቸዉ እየሰራ መሆኑን የተናገሩት አቶ ገመቹ ከሕግ ዉጭ የኢንቨስትመንት መሬት የወሰዱ ወይም የሌሎች ገበሬዎችን ይዞታ ያካለሉ እየመለሱ መሆናቸዉን ጠቅሰዋል። ዞኑ በዚህ ጥረቱ ከጅማ 75 ኪ.ሜ. ላይ በምትገኘዉ በሊሙ-ኮሳ ወረዳ ዉስጥ በሕገ ወጥ መንገድ ለቡናና ለሌሎች ሰብሎች ተብሎ የተወሰደዉን ከ5500 ሄክታር በላይ መሬት መልሰናል ይላሉ። «ወደ 4000 የሚሆን ሄክታር ከሕግ ዉጭ መሬቱን ከወሰዱት ዉስጥ ነዉ ያስመለስነዉ። የቀረዉ ደግሞ ድንበራቸዉን ካሰፉት ከ42 ሰዎች ነዉ የተወሰደባቸዉ። ይህን ሂደት አጠናክረን እንዲህ ዓይነት ሕገ ወጥ ድርጊቶች እንዲወገዱ ከወጣቶች ጋር እየሰራን ነዉ።»
የኦሮሚያ የኢንቨስትመንት ኮሚሽን እንደሚያመለክተዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ከሚመረተዉ ቡና 50 በመቶዉ የሚመረተዉ በኦሮሚያ ክልል ነዉ። ጅማ ዞንን ጨምሮ ጊምቢና ሐረርም ቡና በብዛት የሚመረትበት አካባቢ መሆኑን መረጃዉ ይጠቁማል። ቡና ለኢትዮጵያ ከፍተኛዉን የዉጪ ምንዛሪ የሚያስገኝ ምርት ነዉ።
መርጋ ዮናስ
ነጋሽ መሐመድ