በጋምቤላ ኮሌራ መሰል በተባለ በሽታ የዘጠኝ ሰዎች ሕይወት አለፈ
ሰኞ፣ የካቲት 10 2017
በጋምቤላ ኮሌራ መሰል በተባለ በሽታ የ9 ሠዎች ህይዎት አልፏል
በጋምቤላ ክልል 4 ወረዳዎች «ኮሌራ መሰል» በሽታ መከሰቱን የጤና ባለሙያዎችና ባለሥልጣናት ተናግረዋል፡፡ የበሽታውን ምንነት ለማወቅ ናሙና ወደ አዲስ አበባ መላኩን የጋምቤላ ጤና ቢሮ አስታውቋል፣ እስካሁን በበሽታው ዘጠኝ ሰዎች መሞታቸውን ቢሮው አመልክቷል። በጋምቤላ ክልል ኑዌር ዞን አኮቦ፣ ዋንቱዋ ላሬንና መኮይ በተባሉ ወረዳዎች ካለፍው ሳምንት ጀምሮ «ኮሌራ መሰል» በሽታ ተከስቶ ብዙዎች በህመሙ መጠቃታቸውንና የሞቱም እንዳሉ ለዶይቼ ቬሌ የተናገሩ አስተያየት ሰጪዎች በስልክ ተናግረዋል።
አስተያየታቸውን ከሰጡን የዋንቱዋ ነዋሪዎች መካከል አንዱ በወረዳው በሽታው በከፋ ሁኔታ እየተስፋፋ ነውብለዋል፣ እስካሁን 40 ያክል ሠዎች በበሽታው ሲጠቁ 7 ሠዎች ሞተዋል ብለዋል።
የኑዌር ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ጋትቤል ግርማል በሽታው በቤተሙከራ ባይረጋግጥም ምልክቶቹ የኮሌራ በሽታ እንደሆኑ አመላካች ጉዳዮች እንዳሉ ተናግረዋል፣ ተቅማጥና ማስታወክ የመሳሰሉ የኮሌራ ምልክቶች በበሽተኞች ላይ እንደሚታይ ገልጠዋል። የበሽታውን ምንነት ለማወቅ ናሙና ወደ አዲስ አበባ መላኩንና ውጤት እየተጠበቅ እንደሆነም አስረድተዋል። በበሽታው የ9 ሠዎች ህይወት ማለፉንና የህክምና ባለሙያዎች ለህክምና ወደ አካባቢዎቹ መላካቸውንም ገልጠዋል።
በዋግኽምራ፣ ሳህላ ሰየምት ወረዳ ምንነቱ ያልታወቀ በሽታ ከ5-8 ሰዎችን ገደለ
“በበሽታው 136 ሠዎች ተይዘዋል” የጋምቤላ ጤና ቢሮ
የጋምቤላ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር አቤል አሰፋ ለዶይቼ ቬሌ በስልክ እንደተናገሩት ኮሌራ መሰል በሽታ በክልሉ 4 ወረዳዎች ተከስቷል፣ በሽታው በክልሉ ከተከሰተበት የካቲት 3/2017 ዓ ም ጀምሮ እስከዛሬ 136 ሠዎች በበሽታው ሲያዙ 9 ህይወታቸው አልፏል ነው ያሉት። የሀክምና ባለሙያዎች ወደየወረዳዎቹ በመጓዝ ህክምና እየሰቱ እንደሆነም አብራርተዋል።
የናሙና ውጤት ባይደርሳቸውም የተከሰተው ህመም የኮሌራ በሽታ ስለመሆኑ ማሳያዎችን በመጥቀስ አስረድተዋል።
አሳሳቢዉ የኮሌራ በሽታ ወረርሽኝ በሶማሌ ክልል
“በሽታው ከደቡብ ሱዳን ሳይመጣ አይቀርም” ዶ/ር አቤል አሰፋ
“ ከሁኔታ ትንተና ሲታይ ጉዳዩ ከኮሌራ ጋር ይያያዛል፣ ሁለተኛ በአጎራባች የደቡብ ሱዳን ወረዳ ኮሌራ በቅርቡ ተከስቶ ስለነበር ብዚህ ምክንያት ወደ አኮቦ ጋምቤላ ወረዳ ገብቷል የሚል ከፍተኛ ጥርጣሬአለ” ብለዋል። የኑዌር ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ቧይ ቱት ችግሩ እንዳይስፋፋ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሆነ ተናግረዋል፣ ባለሙያዎችና መድኃኒትም ወደ አካባቢዎቹ ተልኳል ነው ያሉት። የጋምቤላ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር አቤል ህብረተሰቡ የግልና የጋራ ንፅህናውን በመጠበቅ ከበሽታው ራሱን እንዲጠብቅ አሳስበዋል።
ዓለምነው መኮንን
አዜብ ታደሰ
ኂሩት መለሰ