በጋሞ ዞን የዛይሴ ዳንበሌ ጥቃት
ረቡዕ፣ ግንቦት 6 2017
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጋሞ ዞን አርባምንጭ ዙሪያ ወረዳ የምትገኘው የዛይሴ ዳምቢል ቀበሌ ከባለፈው እሁድ ጀምሮ ሰላም እንደራቃት ይገኛል ፡፡ ነዋሪዎች እንደሚሉት በቀበሌው ባለፉት ሦስት ቀናት ብቻ የሰዎች ሞት እና መቁሰል አጋጥሟል ፡፡ አንዲሁም ለጊዜው ቁጥራቸው ያልታወቁ የመኖሪያ ቤቶችም ተቃጥለዋል ፡፡ ታጣቂዎቹ በፀጥታ አባላት ላይ አደረሱት የተባለውን ጥቃት ተከትሎ በአካባቢው አለመረጋጋት መንገሡን ነው ነዋሪዎች ለዶቼ ቬለ የገለጹት ፡፡
የጉዳቱ መጠን
ታጣቂዎቹ በፀጥታ አባላት ላይ አደረሱት የተባለውን ጥቃት ተከትሎ በአካባቢው በተነሳው አለመረጋጋት አንድ የክልሉ የፀጥታ አባልን ጨምሮ አራት ሰዎች መሞታቸውን ዶቼ ቬለ ከታማኝ ምንጮቹ አረጋግጧል ፡፡ የክልሉ የፀጥታ ባለሥልጣናት እስከአሁን ጥቃቱን አሰመልክቶ ያሉት ነገር የለም ፡፡ በታጣቂዎቹ ጥቃት ሕይወቱ ያለፈው አባል ትናንት ቀብሩ ተፈጸሟል ፡፡ አራት የፖሊስ የፀጥታ አባላት ደግሞ በአርባምንጭ ሪፈራል ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው እንደሚገኝ የሆስፒሉ ሥራ አስኪያጅዶክተር አዲስ ተስፋዬ ለዶቼ ቬለ አረጋግጠዋል ፡፡አሳሳቢው የሰብአዊ መብት ጥሰት በጋሞ ዞን
የአለመረጋጋቱ መንስኤ
በቀበሌው አሁን ድረስ ለቀጠለው አለመረጋጋት መንስኤው ማንነታቸው ያልታወቀ ታጣቂዎች በተሽከርካሪ ይጓዙ በነበሩ የፀጥታ አባላት ላይ ጥቃት በመሰንዘራቸው ነው ሲሉ አንድ የአካባቢው ነዋሪ ለዶቼ ቬለ ተናግረዋል ፡፡ አሁድ ጠዋት ፖሊሶች በሦስት የፖሊስ ፒክ አፕ ተሽከርካሪዎች በመጓዝ ላይ እንደነበሩ የጠቀሱት አይን እማኙ “ ይሁንና በድንገት ባደፈጡ ታጣቂዎች ተኩስ ተከፈተባቸው ፡፡ አንድ አባል ሲሞት ሌሎች አራት መቁሰላቸውን አውቃለሁ ፡፡ ጥቃቱን ተከትሎ በቀበሌው በሚገኙ አብዛኞቹ መንደሮች የተኩስ ድምጽ ይሰማ ነበር ፡፡ ትናንትና እና ከትናንት ወዲያ ደግሞ ብዙ ቁጥር ያለቸው የፖሊስ አባላት በቀበሌው ተሠማርተዋል “ ብለዋል ፡፡
በጋሞ ዞን የተፈጸመ የሕጻናት አሰቃቂ ግድያ ኢዜማን ከአካባቢው ባለሥልጣናት ለምን አወዛገበ?
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባሉ አቤቱታ
በዛይሴ ምርጫ ክልል የፌዴራል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ አብረሃም አሞሼ “ የታጠቁ ብድኖች በህግ አስከባሪዎች ላይ ያደረሱት ተግባር መወገዝ ያለበት ነው “ ይላሉ ፡፡ ነገር ግን የፀጥታ አካላቱ የድርጊቱን ፈጻሚዎች ለመያዝ በሚል በሰላማዊ ነዋሪዎች ላይ ጉዳት እያደረሱ እንደሚገኙ የጠቀሱት የምከር ቤት አባሉ “ የፖሊስ አባላቱ ሰላማዊ ነዋሪዎችንና ወጀለኞችን ሳይለዩ ዝም ብለው ይተኩሳሉ ፡፡ በዚህም የሦስት ነዋሪዎች ህይወት አልፏል ፡፡ አሁን ላይ አካባቢው ሥጋት ውስጥ በመውደቁ ሰዎች ለመንቀሳቀስ ጭምር ተቸግረዋል፡፡ በእኛ በኩል የፌዴራሉ መንግሥት የህዝቡን ሥጋት አዳምጦ ምላሽ እንዲሰጥ አቤቱታ አቅርበናል “ ብለዋል ፡፡
ዶቼ ቬለ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባሉ ላቀረቡት ቅሬታ ምላሽ ለማግኘት ወደ ክልሉ ሰላም እና ፀጥታ ቢሮ ሃላፊዎች ቢደውልም ሥልካቸውን ባለመመለሳቸው ምላሻቸውን ማካተት አልተቻለም ፡፡በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጋሞ ዞን በአርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ የሚገኙት የዛይሴ ማህበረሰብ አባላት በልዩ ወረዳ መዋቅር ለመደራጀት የሚያስችላቸውን ጥያቄ እያቀረቡ እንደሚገኙ ይታወቃል ፡፡ የአሁኑ የታጣቂዎች ጥቃት ከዚህ ጥያቄ ጋር የተገናኘ ሥለመሆን አለመሆኑ ግን ማረጋገጥ አልተቻለም ፡፡
ሸዋንግዛው ወጋየሁ
ኂሩት መለሰ
እሸቴ በቀለ