ቢቢሲ የሚታመስበት የቅሌት ተግባር
ሰኞ፣ ኅዳር 3 2005 የብሪታንያ ዜና አገልግሎት ድርጅት ቢቢሲ አንድ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ወግ አጥባቂ እንደራሴ አንድ ግለሰብን በወሲብ ደፍረዋል ሲል ከአሥር ቀን በፊት ባስተላለፈው የተሳሳተ ዜና ሰበብ በገጠመው ቅሌት የተነሳ የቢቢሲ ዋና ኃላፊ ጆርጅ ኤንትዊስል ከሁለት ወራት በፊት የያዙትን ስልጣናቸውን መልቀቃቸው የሚታወስ ነው።
« ባለፉት ጥቂት ሣምንታት የተከሰተው ሁኔታ ቢቢሲ አዲስ መሪ መሰየም አለበት የሚለው ውሳኔ ላይ እንድደርስ ገፋፍቶኛል። » ቲም ዴቪስ አሁን ቢቢሲን በተጠባባቂ ዋና ኃላፊነት እንዲያስተዳድሩ ተሰይመዋል።
በሀሰት የተወነጀሉት የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት እንደራሴ ወቀሳውን ሀሰት ሲሉ ካስተባበሉ በኋላ ወቀሳውን የሰነዘረው ግለሰብም እንደራሴውን በስህተት መወንጀሉን አምኖዋል። የታወቀው ሟቹ የቢቢሲ የቴሌቪዝን አስተዋዋቂ ጂሚ ሳቪል ለብዙ ዓመታት በመቶ የሚቆጠሩ ሕፃናትን በወሲብ ደፍሮዋል በሚል ከተወነጀለ ወዲህ ብዙ ወቀሳ ሲፈራረቅባቸው የቆዩትና ስልጣናቸውን የለቀቁት ኤንትዊስል አሁን 563,000 ዩሮ ማካካሻ ይከፈላቸው መባሉን ወግ አጥባቂ የምክር ቤት እንደራሴዎች ተገቢ ያልሆነ ውሳኔ ነቅፈዋል። ኤንትዊስል ስራቸውን ከለቀቁ በኋላ የዜና ክፍል ኃላፊ ሄለን ቦደን እና ምክትላቸው ስቲቭ ሚቼል ትናንት ከስራ ቦታቸው ለጊዜው መታገዳቸውን ድርጅቱ አስታውቋል። ሁለቱ ግለሰቦች ሳቪል ሕፃናትን መድፈሩን የሚያመላክቱ ጥቆማዎች ባለፈው ዓመ በተደጋጋሚ ቢደርሱዋቸውም ዘገባዎቹን ለማቅረብ ያልፈለጉበት ጉዳይ እስኪጣራ ድረስ ከስራ ቦታቸው እንዲርቁ ታዘዋል።
ይህን ርእሰ ጉዳይ በተመለከተ የለንደንዋነ ዘጋቢአችን ሐና ደምሴን በስልክ አነጋግሬአታለሁ።
ሐና ደምሴ
ተክሌ የኋላ
ነጋሽ መሀመድ