ብሪታኒያ የስደተኞች ቁጥርን ለመቀነስ የጥገኝነት ፖሊሲ ማሻሻያ ማድረጓን አስታወቀች
እሑድ፣ ኅዳር 7 2018
ብሪታኒያ የስደተኞች ቁጥርን ለመቀነስ የጥገኝነት ፖሊሲ ማሻሻያ ማድረጓን አስታወቀች። ማሻሻያው ጥገኝነት ጠያቂዎች የተሻለ ሁኔታ ካለ ወደ ሀገራቸው መመለስን እና የመኖሪያ ፈቃድ የማግኛ ጊዜ ማራዘምን ያጠቃልላል። የብሪታኒያ መንግስት በጥገኝነት ፖሊሲ ላይ ከፍተኛ ለውጦችን ያደረገው እየጨመረ የመጣውን መደበኛ ያልሆነ ስደት ለመቆጣጠር እና በሀገሪቱ እያደገ የመጣውን የቀኝ አክራሪዎች ድጋፍ ለመቀነስ መሆኑን ትናንት ቅዳሜ አስታውቋል።
የዴንማርክን ጥብቅ የጥገኝነት ስርዓት መነሻ በማድረግ በተዘጋጀው በአዲሱ እቅድ መሰረት ወደ እንግሊዝ ለሚገቡ ተገን ጠያቂዎች የሚሰጣቸው የአምስት አመት ፈቃድ ወደ 30 ወር ዝቅ የሚያደርግ ነው። ጥገኝነት የተሰጣቸው ደግሞ የቋሚ የመኖሪያ ፍቃድ ለመጠየቅ አሁን ካለው አምስት አመት ይልቅ 20 አመታትን መጠበቅ አለባቸው።የተሰጣቸው የጥገኝነት ፈቃድ በየጊዜው ተገምግሞ ስደተኞች በሀገራቸው በደህና መኖር ይችላሉ ተብሎ ከታመነ ወደ ትውልድ አገራቸው እንዲመለሱ ይደረጋሉም ተብሏል።የብሪታኒያ የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር «በዘመናችን ትልቁ የጥገኝነት ፖሊሲ ማሻሻያ» ሲሉ ዕቅዱን አወድሶታል ሲል ሮይተርስ የዜና ምንጭ ዘግቧል።
እንደዘገባው በዚህ አመት ብቻ ከ 39,000 በላይ መደበኛ ያልሆኑ ስደተኞች ወደ ሀገሪቱ የገቡ ሲሆን፤ ብዙዎቹ ከሰሜን ፈረንሳይ በትናንሽ ጀልባዎች የተሻገሩ ናቸው። የብሪታኒያ የሃገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ሻባና ማህሙድ ፤«ይህች ሀገር ከአደጋ የሚሸሹትን የመቀበል ኩሩ ባህል አላት። ነገርግን የኛ ልግስና ህገወጥ ስደተኞችን እየሳበ ነው» በማለት ገልፀዋል። ይህም «በማህበረሰቦች ላይ ከፍተኛ ጫና እያሳደረ ነው» ብለዋል።በብሪታንያ የጥገኝነት ጥያቄ እያጨመረ የመጣ ሲሆን እስከ ሰኔ 2025 ዓ/ም ድረስ 111,000 ያህል የጥገኝነት ማመልከቻዎች ቀርበው እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ።
ፀሀይ ጣኔ
እሸቴ በቀለ