ተመላሽ ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች በኢትዮጵያ
ሐሙስ፣ ኅዳር 25 2007 ተመላሾቹ ጊዚያዊ መጠለያ ጣቢያ ለቀናት ከቆዩ በኋላ ከየቤተሰቦቻቸዉ ጋር መቀላቀላቸዉን የገለፁት የዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት የኢትዮጵያ እርንጫፍ ተጠሪ ድርጅታቸዉ ወዶ ተመላሽ ስደተኞችን ከታንዛንያ ብቻ ሳይሆን ከየመንም እየመለሰ ነዉ ነዉ ብለዋል።
ከታንዛንያ በዉዴታ ወደ ሀገራቸዉ ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት ስደተኞች፤ በታንዛንያ ወዶ ተመላሽ ስደተኞችን የሚያግዝ መረሃ-ግብር ከጃፓን መንግሥት ባገኘዉ የገንዘብ ርዳታ መሆኑ ተገልፆአል። ታንዛንያን በማቋረጥ ወደ ደቡብ አፍሪቃ ሊጓዙ ሲሉ ተይዘዉ እስር ላይ እንደነበሩ የተገለፀዉ ተመላሽ ስደተኞች ገሚሱ የእስር ግዚያቸዉን ሳይጨርሱ የታንዛንያ መንግሥት ምህረት አድርጎላቸዉ ለሀገራቸዉ መብቃታቸዉ ተገልፆአል። የዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት «IOM» የህዝብ ግንኙነት ባለሞያ አቶ አለማየሁ ሰይፈስላሴ፤ ድርጅታቸዉ ወዶ ተመላሽ ስደተኞችን ከታንዛንያ ብቻ ሳይሆን ከዚህ ቀደም ከየመንም መልሶአል። ከየመን የተመለሱት ኢትዮጵያዉያን ምን ያህል እንደሆኑ በዉል ቁጥሩን እንደማያዉቁ የገለፁልን የዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት የህዝብ ግንኙነት ባለሞያ አቶ አለማየሁ ሰይፈስላሴ፤ ባለፈዉ ሳምንት መጠናቀቅያ ከታንዛንያ ከተመለሱት 253 ኢትዮጵያዉያን መካከል ሰላሳ ዘጠኙ ለአካለ መጠን ያልደረሱ በመሆናቸዉ የዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት ግዚያዊ ጣቢያ ድጋፍ እና የስነ አይምሮ እገዛ እየተሰጣቸዉ መሆኑን ተናግረዋል። አቶ አለማየሁ ሰይፈስላሴ፤ በቅርቡ ከታንዛንያ ሌሎች በመቶዎች የሚቆጠሩ ስደተኞች ለመመለስ ድርጅቱ ዝግጅት ላይ መሆኑን ገልፀዋል።
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሃመድ