ተቋርጦ የነበረው የህዳሴ ግድብ ድርድር ካይሮ ላይ ተጀመረ
ሰኞ፣ ነሐሴ 22 2015ተቋርጦ የነበረው የህዳሴ ግድብ የሦስትዮሽ ድርድር በትናንትናው ዕለት በግብጽ መዲና ካይሮ መካሄድ ጀመረ። ድርድሩ ከዚህ በፊት በተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች አቡዳቢ ሲደረግ ቆይቶ ረቂቅ ስምምነት ማዘጋጀት ተጀምሮ ሂደቱ መቋረጡ ይታወሳል። የአሁኑ ድርድር በሦስቱ ሃገራት መካከል ትብብርን ለማጠናከር እንደሚረዳ እየተገለጸ ነው።
በሦስትዮሽ ድርድሩ የኢትዮጵያ ተደራዳሪ ቡድን መሪ ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ ትናንት በቲዊተር (X) ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ እና የግብፁ ፕሬዝዳንት አብድል ፈታህ አልሲሲ ከአንድ ወር በፊት በሰጡት መመሪያ መሠረት የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብየውኃ ሙሌት እና አለቃቅ ደንቦችን እና መመሪያዎች የሦስትዮሽ ድርድር በካይሮ መጀመሩን አሳውቀዋል።
ከዚህ በፊት በኢትዮጵያ ተደራዳሪ ቡድን ውስጥ ለአራት ዓመታት ያህል ብቸኛ ሴት ተሳታፊ የነበሩና በአሁን ጊዜ በናይል ቤዚን ኢኒሼቲቭ ሪጂናል አስተባባሪ ሆነው የሚያገለግሉት የድንበር ተሻጋሪ ውኃ ባለሙያዋ ዶ/ር ኢንጂነር አዳነች ያሬድ ስለረጂሙ የሃገራቱ ድርድር ሂደት በሰጡን ቃለምልልስ ከአሞላሉ መጠንና የጊዜ ሂደት ጋር የተያያዙ ልዩነቶች ስምምነቱ እንዳይቋጭ እቅፋት ሆኖ መቆየቱን አንስተዋል።
በካይሮ የቀጠለው የህዳሴ ግድብ ድርድር
የኢትዮጵያ ተደራዳሪ ቡድን መሪው ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ በዚሁ መድረክ የመክፈቻ ፕሮግራም ባደረጉትም ንግግር የሦስትዮሽ ድርድሩ የኢትዮጵያን የአሁንና የወደፊት ትውልድ ጥቅም ለማስጠበቅ በአባይ ውኃ የመጠቀም መብት መሠረታዊ መሆኑን ጠቁመዋል። ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ ግድቡ ለሦስቱ ሃገራት የሚሰጠው ጥቅም ከፍተኛ መሆኑንም አመልክተው፤ ኢትዮጵያ በፍትሃዊ እና ምክንያታዊ ተጠቃሚነት መርህ ላይ የተመሰረተ አቋሟን አጠናክራ ትቀጥላለችም ብለዋል።
ግብጽ በበኩሏ ትናንት እሑድ ኢትዮጵያ እና ግብጽን ሲያወዛግብ ቆይቶ ተቋርጦ የነበረው የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሦስትዮሽ ድርድር ከቆመበት መቀጠሉን ማሳወቋን ኤ.ኤፍ.ፒ ዘግቧል። ባለፈው ሐምሌ ወር በካይሮ በሱዳን ጉዳይ ከመከረው ከአፍሪካ መሪዎች ስብሰባ ጎን ለጎን የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ እና ሬዝዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ በአራት ወራት ውስጥ ግድቡን በሚመለከት ከስምምነት ለመድረስ በሚያስችል አግባብ ላይ መወያየታቸው አይዘነጋም። ትናንት በግብጽ ካይሮ በተጀመረው የሦስትዮሽ ድርድሩ ላይ የግብጽ፣ ኢትዮጵያ እና ሱዳን ተወካይ ልዑካን መታደማቸውም ተዘግቧል፡፡ በ2003 ዓ.ም. መጋቢት 24 የመሠረት ድንጋይ ተቀምጦለት ወደ ሥራ የገባው የአፍሪካ ትልቁ የኤሌክትሪክ ማመንጫ ፕሮጀክት ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላለፉት 12 ዓመታት ኢትዮጵያ እና ግብጽን በጉልህ ሲያወዛግብ ብቆይም እስካሁን ይህ ነው የሚባል ስምምነት ላይ መድረስ አልተቻለም። ይሁንና ባለፉት ሦስት ተከታታይ ዓመታት ውኃ በመያዝ ባለፈው የካቲት ወር ከግድቡ ኃይል ማመንጨት መጀመራን ያሳወቀችው ኢትዮጵያ በዚህም ዓመት የውኃ መያዝ ሂደቱ እንደሚቀጥል አስቀድሞ በሰኔ ወር ማሳወቋ ይታወሳል።
ሥዩም ጌቱ
ሸዋዬ ለገሠ
ነጋሽ መሀመድ