1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

ተፈናቃይ ገበሬዎች እርሻ ጀመሩ

ሐሙስ፣ ሰኔ 22 2015

በመጋቢት ወር 2014 ዓ.ም በካማሺ ዞን በታጣቂዎች እና መንግስት መካከል የዕርቅና የሠላም ስምምነት መደረሱን ተከትሎ ተፈናቅሎ በየመጠለያ ጣቢያው የነበሩ ሰዎች ወደየ ቀድሞ ቤታቸው መመለሳቸውን ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች ተናግረዋል

 Kamashi town in Benishangul Gumuz region Ethiopia
ምስል፦ Negassa Dessalegn/DW

የማደበሪያ እጥረት መኖሩን የክልሉ ግብርና ቢሮ አረጋግጧል

This browser does not support the audio element.

ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በመጠለያ ጣቢያ የቆዩና ወደ ቀያቸው የተመለሱ ዜጎች በግብርና ስራ መሰማራታቸውን አስታወቁ፡፡ ወደ ቤታቸው ተመልሰው በእርሻ ስራ የተሰማሩ ነዋሪዎች የሚፈለገውን ያህል ባይሆንም የታረሰውን መሬት በዘር ለመሸፈን የአፈር ማዳበሪያ ችግር እንዳገጠማቸው እየገለጹ ነው፡፡ የክልሉ የግብርና ቢሮ በበኩሉ ዘንድሮው የምርት ዘመን በተሻለ መልኩ አርሶ አደሩ በክልሉ ስር በሚገኙ 3ቱም ዞኖች ወደ መግባቱን ገልጾ የአፈር ማዳበሪያ እጥረት እንዳለም ጠቁመዋል፡፡ በዚህ ምርት ዘመን 29 ሚሊዩን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱንም የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊው አቶ ባበክር ሀሊፋ ጠቁመዋል፡፡ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በ2013 ዓ.ም 475ሺ ህዝብ ተፈናቅሎ የቆየበት ሲሆን ከግንቦት 2014 ዓ.ም አንስቶ ወደየ ቀድሞ ቀያአቸው መመለሳቸውን የክልሉ መንግስት ከዚህ ቀድም ይፋ አድርጓል፡፡

በመጋቢት ወር 2014 ዓ.ም በካማሺ ዞን በታጣቂዎች እና መንግስት መካከል የዕርቅና የሠላም ስምምነት መደረሱን ተከትሎ ተፈናቅሎ  በየመጠለያ ጣቢያው የነበሩ ሰዎች ወደየ ቀድሞ ቤታቸው መመለሳቸውን ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡ በካማሺ ዞን አጋሎ እና ያሶ ከተባሉ ቦታዎች ተፈናቅለው ለአንድ ዓመት ያህል  በዞኑ ዋና ከተማ እንደ ቆዩ የነገሩን አቶ ወርቁ ጉዴታ እና አቶ ታጁ ከበደ ባሁኑ ወቅት ወደየ ቀያአቸው ተመልሰው መደበኛ ስራቸውን ጀምረዋል፡፡ በግብርና ስራ ላይ ተሰማርቶ የሚገኙ ሲሆን ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸርም በርካታ ሄክታር መሬት መታረሱን ገልጸዋል፡፡ ሆኖም በየወረዳቸው በግብርና ስራ ለተሰማሩ ሰዎች አስፈላጊውን የምርጥ ዘር እና የአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት አለመደረጉን አመልክተዋል፡፡ በሌላ በኩል ባለፈው ዓመት በበቂ ሁኔታ ባለመታረሱ ሰዎች ሰብአዊ ድጋፍ እንደሚሹም አክለዋል፡፡ 

አቶ በለጠ የተባሉ የመተከል ዞን ማንዱራ ወረዳ ነዋሪም በተመሳሳይ የአፈር ማዳበሪያ እጥረት መኖሩን ገልጸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የምርት ዘር አቅርቦት  የለም ብሏል፡፡ የአፈር ማዳበርያ ዋጋ በእጅጉ መጨመሩንና በኩንታል እስከ 10ሺ ብር  እየተገዛ እንደሚገኝ አብራርተዋል፡፡ በአካባቢአቸው ይስተዋል የነበረው የጸጥታ ችግርም መሻሻሉንና በወረዳቸው አርሶ አደሩ ከዚህ ቀደም ከነበረው በተሻለ መልኩ ወደ ስራ መግባቱንም ተናግረዋል፡፡

በኒሻንጉል ጉሙዝ ከሚገኙ መጠለያ ጣቢያዎች አንዱምስል፦ Negassa Dessalegn/DW

የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ባበክር ሀሊፍ በሰጡን ማብራሪያ በክልል ደረጃ የማዳበሪያ እጥረት እንዳለ አረጋግጠዋል፡፡ ለክልሉ የቀረበው የአፈር ማዳበሪያ መጠን በ44 በመቶ ቀንሶ የመጣ በመሆኑ ሊዳረስ አልቻለም ብሏል፡፡ አርሶ አደሩ እንደ ኮምፖስት ያሉ አማራጭ ማዳበሪያ እንዲጠቀሙ ተቋማቸው ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝም ገልጸው  በክልሉ እስካሁን በአሶሳ፣መተከል እና ካማሺ  5 መቶ ሺ ሄክታር መሬት በዘር መሸፈኑን ተናግረዋል፡፡

በ2014 ዓ.ም ምርት ዘመን በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል 1.1 ሚሊዩን ሄክታር መሬት በምርት ለመሸፈን ታቅዶ የነበረ ሲሆን 843ሺ ያህሉ ሄክታር መሬት  በምርት መሸፈኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አመልክተዋል፡፡ በዘንድሮ የምርት ዘመን  ደግሞ 937ሺ ሄክታር በምርት ይሸፈናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ነጋሳ ደሳለኝ

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሰ

 

 

 

 

 

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW