1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቱርክና የኩርዶች ጥቃት

ሰኞ፣ ጥቅምት 11 2000

«ጎረቤት አገር የአሸባሪዎች መሸሸጊያ ከሆነች እኛም ዓለም ዓቀፉን ህግ የመጠቀም መብት አለን ።» የቱርክ ጠቅላይ ሚኒስትር ሬሴፕ ተይፕ ኤርዶጋን

ልጃቸው በፒኬኬ የተገደለባቸው ቤተሰቦች ከሟች ፎቶግራፍ ጋር
ልጃቸው በፒኬኬ የተገደለባቸው ቤተሰቦች ከሟች ፎቶግራፍ ጋርምስል AP

አስራ ሁለት የቱርክ ወታደሮች ትናንት በኢራቅ ወሰን አቅራቢያ በኩርድ አማፅያን መገደላቸው የቱርክን ህዝብ አስቆጥቷል ። መንግስት ድንበር ተሻግሮ አማፅያኑ ወደ ሚገኙበት ወደ ኢራቅ በመዝለቅ ግድያውን በፈፀሙት የኩርድ አማፅያን ላይ የአፀፋ ዕርምጃ እንዲወስድ ህዝቡ ግፊት እያደረገ ነው ። ዩናይትድ ስቴትስ ደግሞ ቱርክ ይህን ከማድረግ እንድትቆጠብ መምከርዋን ቀጥላለች ። በዚህ አጣብቂኝ ውስጥ ያሉት የቱርክ ጠቅላይ ሚኒስትር ሬሴፕ ተይፕ ኤርዶጋን በበኩላቸው መንግስታቸው በዓለም ዓቀፍ ህግጋት መሰረት ለሚወስዳቸው ዕርምጃዎች ከማንም ፈቃድ ማግኘት አያሻውም ይላሉ ። አስራ ሁለቱ የቱርክ ወታደሮች የተገደሉት በእንግሊዘኛው ምህፃር ፒኬኬ በመባል በሚጠራው የኩርድ ሰራተኞች ፓርቲ አማፅያን ነው ። በቱርክ ወታደሮች ላይ ይህን መሰሉ ጥቃት የደረሰው ከሰሜን ኢራቅ በሚንቀሳቀሱት በፒኬኬ አማፅያን ላይ መንግስት ወታደራዊ ዕርምጃ እንዲወሰድ የቱርክ ፓርላማ በተስማማ በአራተኛው ቀን መሆኑ ነው ። በትናንቱ ግድያ ቱርኮች ክፉኛ ተበሳጭተዋል ። የቱርክ ኃይል ድንበር ተሻግሮ እንዲያጠቃ መንግስት ትዕዛዝ እንዲያስተላልፍ ጩኽታቸውን እያሰሙ ነው ። ዛሬ በቱርክ ትልቂቱ ከተማ ኢስታንቡል ውስጥ አደባባይ የወጡ ወደ ሶስት ሺህ የሚጠጉ ተቃዋሚዎች ፒኬኬን ሲያወግዙ መንግስት አፋጣኝ ወታደራዊ ዕርምጃ ባለመውሰዱ ወቅሰዋል ። ከዚያም አልፈው የኤርዶጋን መንግስት ሀላፊነቱን በቅጡ ባለመወጣቱ ስልጣን እንዲለቅም ጠይቀዋል ። የተቃውሞ ሰልፉ በኢስታንቡል ብቻ አልነበረም ። በዋና ከተማይቱ በአንካራ እንዲሁም በወደብ ከተማዋ በሜርሲንም ተመሳሳይ ሰልፎች ተካሂደዋል ። ከህዝቡ በኩል ይህን መሰሉ ግፊት የሚደረግባቸው የቱርኩ ጠቅላይ ሚኒስትር ኤርዶጋን ከዩናይትድ ስቴትስ በኩል ደግሞ ሌላ ጫና ገጥሟቸዋል ። ቱርክ በአማፅያኑ ላይ ዕርምጃ ከመውሰድ እንድትታገስ ዩናይትድ ስቴትስ ጠይቃለች ። የዩናይትድ ስቴትሱ መከላከያ ሚኒስትር ሮበርት ጌትስ እንዳሉት ቱርክ በፒኬኬ ላይ ሰፊ ወታደራዊ ዘመቻ ማካሄዷ ራስዋንም ሆነ ማንንም አይጠቅምም ።
ድምፅ ................................
“ድንበር ተሻጋሪ ሰፊ ዘመቻ መካሄዱ ከቱርክ ከኛም እንዲሁም ከኢራቅም ጥቅም ጋር የሚቃረን ነው የሚሆነው “
ጠቅላይ ሚኒስትር ስለ ሁኔታው ከዩናይትድ ስቴትስዋ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኮንዶሊሳ ራይስ ጋር ትናንት በስልክ ባካሄዱት ውይይት ሰሜን ኢራቅ በሚገኙት የፒኬኬ አማፅያን ላይ ዋሽንግተን የበኩልዋን ዕርምጃ እንድትወስድ ጠይቀው ነበር ። ይሁንና ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያገኙት መልስ ግን ታገሱ የሚል ነው ። ኤርዶጋን ለጋዜጠኖች እንደተናገሩት የጥቂት ቀናት ጊዜ ስጡን ነው የተባሉት ። ብሪታኒያ ደግሞ በቱርክ ወታደሮች ላይ የተፈፀመውን ጥቃት አውግዛ ቱርክ ከኢራቅ ጋር መፍትሄ ሊያመጣ የሚችል ውይይት እንድታካሂድ ሀሳብ አቅርባለች ። ሆኖም ኤርዶጋን በዚሁ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት ለዚህ ሁሉ ትዕግስቱ ያላቸው አይመስልም ። ጎረቤት አገር የአሸባሪዎች መሸሸጊያ ከሆነች እኛም ዓለም ዓቀፉን ህግ የመጠቀም መብት አለን ። ለዚህም ከማንም ፈቃድ ማግኘት አይጠበቅብንም ነው ያሉት በጋዜጣዊ መግለጫቸው ። እንደርሳቸው ፒኬኬን አሸባሪ ከማይል መንግስት ጋር መደራደርም አይሹም ።
ድምፅ
“ፒኬኬን እንደ አሸባሪ ድርጅት ከማያይ መንግስት ጋር ቱርክ አትነጋገርም ። “
የአውሮፓ ህብረት በበኩሉ ቱርክ በፀረ ሽብሩ ዘመቻ ያላትን አቋም እንደሚደግፍና ከጎንዋም እንደሚቆም አስታውቋል ። ይሁንና አንካራ ፒኬኬን ለማጥቃት ወታደሮችዋን ወደ ኢራቅ እንዳትልክ ከማስጠንቀቅ ወደ ኃላ አላለም ። የቱርክ ወታደራዊ ባለስልጣናት እንደተናገሩት ትናንት አማፅያኑ ካደረሱት ጥቃት በኃላ በተወሰደው ዕርምጃ ከአማፅያኑ ወገንም ወደ ሰላሳ ሁለት የሚሆኑ ተገድለዋል ።

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW