ቱርክ የሩስያን የጦር ጄት መታ ጣለች
ማክሰኞ፣ ኅዳር 14 2008የቱርክ ጦር ሠራዊት ዛሬ ከቀትር በፊት ሶርያ ድንበር አቅራብያ ሱ 24 ተብሎ የሚታወቅ አንድ የሩስያ የጦር ጀት መቶ መጣሉን ቱርክ አስታውቃለች። ክልሌ ተጥሷል ስትል የገለፀችዉ ቱርክ ከተደጋጋሚ ማስጠንቀቅያ በኋላ አውሮፕላኑን መተው የጣሉት ሁለት F16 የቱርክ ተዋጊ ጀቶችዋ መሆናቸውን ማመልከትዋ ተዘግቧል።
ሩስያ በበኩልዋ አዉሮፕላኑ በሶርያ የአየር ክልል ዉስጥ፣ ከቱርክ ድንበር አንድ ኪሎሜትር ርቀት ላይ የነበረና ሶርያ አየር ክልል ዉስጥ ከድንበሩ አራት ኪሎሜትር ርቀት ላይ መዉደቁን በመግለጽ የቱርክን ዘገባ አስተባብላለች። የሩስያ መንግሥት አዉሮፕላኑ ተመቶ መዉደቁ ከፍተኛ መዘዝ እንደሚያስከትከትል አስታዉቋል። ፕሬዚዳንት ፑቲን ሁኔታዉ ከጀርባ በኩል የተሰነዘረ ዱላ ነዉ ሲሉ መናገራቸዉን ዜና ምንጭ «ሮይተርስ» ዘግቦአል።
የሩስያዉን አዉሮፕላን ያበሩ የነበሩት ሁለት ፓይለቶች እስካሁን የደረሱበት ቦታ በዉል ባይታወቅም፤ የሩስያ መከላከያ ሚኒስቴር አዉሮፕላኑ ተመቶ እንደወደቀ በሰጠዉ መግለጫ ሁለቱም የአዉሮፕላኑ አብራሪዎች በጃንጥላ ለመዉረድ እንደቻሉ አስታውቆ ነበር። በሶርያ የአማጽያን ተወካዮችና የሶርያ መንግሥት ተቃዋሚዎች ለፈረንሳዩ የዜና ወኪል አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ እንደገለፁት አንዱ ፓይለት ሞትዋል አንዱ ደግሞ የደረሰበት አይታወቅም። ይህ በእንዲህ እንዳለ «ናታሊ» የተሰኘ አንድ የሩስያ የንግድና የጉዞ ወኪል ወደ ቱርክ የሚደረግ ማንኛዉንም ጉዞና ንግድ ማቋረጡን አስታዉቋል።
በሌላ በኩል የሩስያ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ ወደ ቱርክ የነበራቸዉን ጉዞ መሰረዛቸዉን ቃላቀባያቸዉ አስታዉቀዋል።
አዜብ ታደሰ
እሸቴ በቀለ