ችግሩ «በቤተክርስቲያኗ ቀኖና መሰረት ተፈቷል» ቅዱስ ሲኖዶስ
ረቡዕ፣ የካቲት 8 2015
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስና «የኦሮሚያና ብሔር ብሔረሰቦች ሲኖዶስ» በማቋቋማቸው በተወገዙት ሦስት ሊቃነ ጳጳሳት መካከል የተፈጠረው ችግር በቤተክርስቲያኗ ቀኖና መሰረት ተፈቷል ሲሉ ብጹእ አቡነ አብርሃም የጠቅላይ ቤተ ክህነት ስራ አስኪያጅ ዛሬ ማምሻውን አስታውቀዋል። ለቤተክርስቲያን አንድነት ጠቅላይ ሚንሥትር ዐቢይ አሕመድ አደረጉት ላለው አስተዋጽኦ ቅዱስ ሲኖዶሱ ምሥጋናውን አቅርቧል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ አቡነ አብርሃም «የቤተክርስቲያን ጩኸት ተሰምቷል» በማለት መግለጫውን ሲያሰሙ ተናግረዋል። የቅዱስ ሲኖዶሱ መግለጫ የተከፈተው በርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት አቡነ ማቲያስ ሲሆን፦ «ምሕረት እና እውነት ተገናኙ» ሲሉ ነበር ንግግራቸውን የጀመሩት። ቀደም ሲል፦ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በዛሬ የዜና እወጃው ጠቅላይ ሚንሥትር ዐቢይ አህመድ፣ የመከላከያ ሚኒስትሩ እና ሌሎች ከፍተኛ ባለሥጣናት እንዲሁም የሀገር ሽማግሌዎች ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ጋር ሲተቃቀፉ እና ሲጨባበጡ ዐሳይቷል። ተወግዘው የነበሩት ሦስቱ ሊቃነጳጳሳት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትሪያርክ አቡነ ማቲያስንና ሌሎች ሊቃነ ጳጳሳትን እጅ ሲነሳሱና ሰላምታ ሲለዋወጡም በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ታይተዋል።
ሥዩም ጌቱ
ሸዋዬ ለገሠ