ናይጄሪያ ወደቦቿ ከብሪታንያ ብዙ ያተርፋሉ ስትል አቅዳለች
ቅዳሜ፣ መጋቢት 19 2018
ባለፈው ሳምንት የናይጄሪያ ፕሬዚደንት ቦላ ቲንቡ የአገራቸው ዋነኛ የንግድ ወደቦችን ለማሻሻል ቃል የገባችው ብሪታንያን ጎብኝተው ነበር ። ምዕራብ አፍሪቃዊቷ ናይጄሪያ፦ ከአንድ ክፍለ ዘመን በፊት የብሪታንያ ቅኝ ግዛት በነበረችበት ጊዜ የተገነባው የአገሪቱ ዋነኛ የንግድ ማሳለጪያ አፓፓን ጨምሮ የቲንካን ደሴት ወደቦችን ለማሻሻልም ከፍተኛ ተስፋ ሰንቃለች ።
860 ሚሊዮን ዩሮ ያወጣል የተባለው የወደቦቹ ማስፋፊያ መዋእለ ንዋይ ፍሰት ድጋፍ የሚደረገው በብሪታንያ የሸቀጦች ላኪ ኩባንያ ነው ። የናይጄሪያ የባሕር እና የሰማያዊ ኤኮኖሚ ሚንስትር አዴግቦዬጋ ኦዬቶላ፦ ማሻሻያው እጅግ ለውጥ የሚደረግበት መሆኑን ይፋ አድርገዋል ።
በእርግጥም የናይጄሪያ ወደቦችን ሠንቆ የያዘው የሎጂስቲክ ችግር ብርቱ ተግዳሮት መሆኑ ይነገራል ። የኤኮኖሚ ተንታኙ ኢኬሜስቲ ኤፊዮንግ የችግሩን ጥልቀት እንዲህ ያብራራሉ ።
«በአሁኑ ወቅት የናይጄሪያ ወደቦች አስተማማኝ መተላለፊያ ከመሆን ይልቅ፤ ውድ መሆናቸው ነው የሚታየው ። ከመሠረተ ልማቱ ጥያቄ ባሻገር ቁልፍ የውኃ ማገጃ ግድግዳዎቹ መደርመሳቸው እና የመርከብ መተላለፊያዎቹ ጥበት ጥያቄ የሚነሳባቸው ናቸው ። ዋነኛ ችግሮቹ ስልታዊ ናቸው ። ሙስና አለያም ቢሮክራሲያዊ ኪራይ ሰብሳቢነትን አለያም የከባድ ተሽከርካሪዎችን ፍሰት የተቆጣጠሩ የተደራጁ ማፊያዎችን በቅጽበት ማስወገድ አይቻልም ። ስለዚህ እነዚያን ሥልታዊ ተግዳሮቶች ሳይጋፈጡ ይህ የ1 ቢሊዮን ዶላር መዋእለ ንዋይ ፍሰት በቀላሉ በተመሳሳይ የትራፊክ መጨናነቅ ላይ የተደላደለ መንገድ እንደመገንባት ማለት ነው ።»
በርዝመቱ የታወቀ 853 ኪሎ ሜትሮች ግድም የባሕር ጠረፍ ባለቤቷ ናይጄሪያ ሰባት ዋና ዋና ወደቦች አሏት ። ከሁሉም ወደቦች የሌጎስ ወደብ 80 በመቶ የአገሪቱ ሸቀጦች ከውጭ የሚገቡበት ነው ።
የመሠረተ ልማት መበላሸት፣ የመርከቦችን ብዛት የሚገድቡ ጥልቀት የሌላቸው የውኃ መተላለፊያዎች፣ እና ከፍተኛ የደሕንነት ወጪዎች እና የቢሮክራሲ መዘግየቶች ብዙውን ጊዜ አስመጪዎች በጎረቤት አገራት ቤኒን፣ ቶጎ እና ጋና ውስጥ የበለጠ ቀልጣፋ ወደቦችን እንዲጠቀሙ ያስገደዳሉ ።
ሚኒስቴር አዴግቦዬጋ ኦዬቶላ እንዳሉት ከሆነ ግን ወደቦቹን ለማሻሻል ከብሪታንያ ጋር የተደረገው ስምምነት እጅግ ወሳኝ ነው ። ስምምነቱ ወደቦቹን ወደ ዲጂታል በመቀየር እና በራሳቸው ማለትም አውቶማቲክ እንዲሠሩ በማድረግ የናይጄሪያን ገቢ እና ወጪ ለማቀላጠፍ ሚናው የላቀ ይሆናል ።
በስምምነቱ መሠረት፦ የብሪታንያ ኩባንያዎች ቢያንስ 272 ሚሊዮን ዩሮ ያገኛሉ ። ብሪታንያ 80 ሚሊዮን ዩሮ የሚያወጡ 120,000 ቶን ብረቶችን ማስገባቷም የስምምነቱ አካል ነው ተብሏል ። ስምምነቱ ተቃውሞ ማጫሩ አልቀረም ። የናይጄሪያ ተቃዋሚው የአፍሪቃ ዲሞክራሲ ጉባኤ ጥምረት (ADC) ስምምነቱን ለብሪታንያ ያደላ ያልተመጣጠነ ሲል ተችቷል ።
ከተቃውሞው ባሻገር የብሪታንያ መዋእለ ንዋይ የናይጄሪያ ወደቦችን በእርግጥ ካሉበት ችግር ያወጣል የሚለው ነው? ጊዜ ይፈታዋል ።
አቢዮዱን ጃሚዩ/ማንተጋፍቶት ስለሺ
እሸቴ በቀለ