ንኮሳዛና ድላማኒ ዙማ
ማክሰኞ፣ ሐምሌ 10 2004አዲሷ የአፍሪቃ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ደቡብ አፍሪቃዊቷ ኒኮሳዛና ድላማኒ ዙማ የአፍሪቃ ክፍለ ዓለምን ህብረት ለማጠናከር ቃል ገቡ ። ከአወዛጋቢ ድምፅ አሰጣጥ በኋላ በጠባብ ልዩነት ለዚህ ሃላፊነት የበቁት ድላማኒ ዙማ አፍሪቃውያንን ይበልጥ ለማግባባት በተያዘው ጎዳና ስራቸውን እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል ። ለህብረቱ ኮሚሽን ፕሬዝዳንትነት ያበቃቸው ድልም የግላቸው ሳይሆን በአጠቃላይ የአፍሪቃ ድል ተደርጎ መታየት እንደሚገባውም ተናግረዋል ። ደቡብ አፍሪቃዊቷ ኒኮሳዛና ድላማኒ ዙማ ለትላልቅ ተግዳሮቶችና ለአዲስ ሥር ጅምር እንግዳ አይደሉም ። በፀረ አፓርታይድ ዘመን የነፃነት ታጋይ ነበሩ ። ሁሉንም ዘር ባሳተፈ የመጀመሪያው ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ሥልጣን በያዙት በኔልሰን ማንዴላ አስተዳደር ካቢኔ ውስጥ የመጀመሪያዋ የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ነበሩ ። ማንዴላን በተኩት በታቦ ኤምቢኪ ካቢኔም በ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት ለ 10 ዓመታት ያገለገሉ የመጀመሪያዋ ሴት ሚኒስትርም ናቸው አሁንም በአዲሱ ሃላፊነታቸው የመጀመሪያዋ ሴት የአፍሪቃ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር በመሆን ሥራቸውን በልበ ሙሉነት ነው የሚያያዙት ።
« በማንኛውም የስራ ደረጃ እንዳገለገልኩት ነው አሁንም የማገለግለው ። ሆኖም ግልፅ ነው በክፍለ ዓለማችን ሴቶች አሁንም ቢሆን ነፃ እንዳልሆኑ አልረሳም »
ለብዙ አፍሪቃውያት አርአያ የሆኑት የ63 ዓመቷ ድላማኒ ዙማ በተፎካካሪዎቻቸውም ዘንድ አልፎ አልፎ ንቅንቅ የማይል ፅኑ አቋም እንዳላቸው ዓላማቸውን ለማራመድ ወሳኝ እርምጃ በመወስድ ነው የሚታወቁት ። በተፈጥሮአቸውው ታጋይ ናቸው ። አስቀድሞም የፖለቲካ ዝንባሌ የነበራቸው ድላማኒ በለጋ እድሚያቸው የደቡብ አፍሪቃው ብሔራዊ ምክር ቤት አባል ሆኑ ። በሃያ ዎቹ አጋማሽ እድሜያቸው ላይም የትውልድ አካባቢያቸውን የክዋዙሉ ናታልን ክፍለ ግዛት ለቀው ወደ ብሪታኒያ ተሰደዱ ። በብሪታኒያም ህክምና እየተማሩ ከትምህርቱ ጎን ለጎን በፀረ አፓርታይድ እንቅሳቃሴ ይሳተፉ ነበር ። እጎአ በ1982 ከአሁኑ የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዝዳንት ጄኮብ ዙማ ጋር ትዳር መስርተው 4 ልጆች አፍርተዋል ። ከ 16 ዓመታት በኋላ ፣ በ 1998 ከጄኮብ ዙማ ጋር ተለያዩ ። በማንዴላ ካቢኔ በጤና ሚኒስትርነት ጥሩ ስም ያተረፉት ድላማኒ ዙማ ከባለቤታቸው ጋር በተለያዩ በዓመቱ የመጀመሪያዋ ሴት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው ተሾሙ ።
በዚሁ ሃላፊነታቸው በኮንጎ ዲሞክራሲያዊት ሪፕብሊክ የሰላም ድርድር በሸምጋይነት ባደረጉት አስተዋጽኦ ይወደሳሉ ። ይሁንና የዚምባብዌ ፕሬዝዳንት ሮበርት ሙጋቤ ተግባራዊ ባደረጉትና በሺህዎች የሚቆጠሩ ነጭ ገበሬዎችን በኃይል ባፈናቀለው የመሬት ይዞታ ማሻሻያ ላይ አንዳችም ወቀሳ ባለመሰንዘር ይተቻሉ ። እጎአ በ2009 ጄኮብ ዙማ የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዝዳንት ሲሆኑ የቀድሞ ባለቤታቸው ድላማኒ ዙማ የሃገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ሆኑ ። በአዲሱ ሃላፊነታቸውም ከከፍተኛ ሥልጣን ዝቅ እንደተደረጉ ነበር የፖለቲካ ታዛቢዎች አስተያየታቸውን የሰጡት ። ድላማኒ ዙማ ግን ሃላፊነቱን እንደወሰዱ የመስሪያ ቤቱን ያልጸዳ አሰራር ማስተካከል ላይ ነበር ያተኮሩት ። « ሙሰኛ ባለሥልጣናት ከክፍሉ መሰናበት አለባቸው ። በማንኛውም ደረጃ ቢሆን ሙሰኛ ባለሥልጣንን ቸል ልንል አይገባም ። ሁላችንም ታማኝ መሆን አለብን ፤ ሥራችንንም በታማኝነት ማከናወን ይገባናል ።»
ድላማኒ ዙማ ያሉትን በተግባር የሚተረጉሙ መሆናቸውን በተለያዩ ጊዜያት አስመስክረዋል ። የሃገር አስተዳደር ሚኒስቴር በታሪኩ የሂሳብ መርማሪዎች ጥፋት ያላገኙበት በርሳቸው የሥልጣን ዘመን ነው ። ለአዲሱ ሃላፊነታቸውም የፖለቲካ ተሞክሮአቸው ፣ የማያወላውል አቋማቸውን ፣ ዲፕሎማሲ ክህሎታቸው ጠቃሚ ነው ። እንደ አፍሪቃ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበርነታቸው የተሰነጣጠረውን የአባል መንግሥታቱ አቋም አሰተባብረው ድርጅቱ አንድ አቋም እንዲይዝና በዛ ያሉት የክፍለ ዓለሙን አንገብጋቢ ችግሮች መፍትሄ ያገኙ ዘንድ የተላለፉ ውሳኔዎች ተገባራዊ እንዲሆኑ ማብቃት ይጠበቅባቸዋል ። ለእነዚህ ተግዳሮቶች መፍትሄ ለመሻት ወይዘሮ ድላማኒ ዙማ ብቃቱ እንዳላቸው ደቡብ አፍሪቃውያን ይተማመኑባቸዋል ።
ሂሩት መለሰ
ነጋሽ መሐመድ