1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ንኮሳዛና ድላማኒ ዙማ

ማክሰኞ፣ ሐምሌ 10 2004

አዲሷ የአፍሪቃ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ደቡብ አፍሪቃዊቷ ኒኮሳዛና ድላማኒ ዙማ የአፍሪቃ ክፍለ ዓለምን ህብረት ለማጠናከር ቃል ገቡ ። ከአወዛጋቢ ድምፅ አሰጣጥ በኋላ በጠባብ ልዩነት ለዚህ ሃላፊነት የበቁት ድላማኒ ዙማ አፍሪቃውያንን

epa03307523 Nkosazana Dlamini-Zuma of South Africa leaves the room after giving a press conference during the 19th African Union Summit in Addis Ababa, Ethiopia, 15 July 2012. South Africa's home affairs minister Nkosazana Dlamini-Zuma is challenging incumbent Jean Ping of Gabon for the bloc's top job after both of them failed to win the required two-thirds majority of the vote at the last summit. If the election fails again this time, it could leave Ping in position until the next summit in January 2013. EPA/MARTIN DIXON +++(c) dpa - Bildfunk+++
ምስል picture-alliance/dpa

አዲሷ የአፍሪቃ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ደቡብ አፍሪቃዊቷ ኒኮሳዛና ድላማኒ ዙማ የአፍሪቃ ክፍለ ዓለምን ህብረት ለማጠናከር ቃል ገቡ ። ከአወዛጋቢ ድምፅ አሰጣጥ በኋላ በጠባብ ልዩነት ለዚህ ሃላፊነት የበቁት ድላማኒ ዙማ አፍሪቃውያንን ይበልጥ ለማግባባት በተያዘው ጎዳና ስራቸውን እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል ። ለህብረቱ ኮሚሽን ፕሬዝዳንትነት ያበቃቸው ድልም የግላቸው ሳይሆን በአጠቃላይ የአፍሪቃ ድል ተደርጎ መታየት እንደሚገባውም ተናግረዋል ። ደቡብ አፍሪቃዊቷ ኒኮሳዛና ድላማኒ ዙማ ለትላልቅ ተግዳሮቶችና ለአዲስ ሥር ጅምር እንግዳ አይደሉም ። በፀረ አፓርታይድ ዘመን የነፃነት ታጋይ ነበሩ ። ሁሉንም ዘር ባሳተፈ የመጀመሪያው ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ሥልጣን በያዙት በኔልሰን ማንዴላ አስተዳደር ካቢኔ ውስጥ የመጀመሪያዋ የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ነበሩ ። ማንዴላን በተኩት በታቦ ኤምቢኪ ካቢኔም በ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት ለ 10 ዓመታት ያገለገሉ የመጀመሪያዋ ሴት ሚኒስትርም ናቸው አሁንም በአዲሱ ሃላፊነታቸው የመጀመሪያዋ ሴት የአፍሪቃ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር በመሆን ሥራቸውን በልበ ሙሉነት ነው የሚያያዙት ።

ምስል AP

« በማንኛውም የስራ ደረጃ እንዳገለገልኩት ነው አሁንም የማገለግለው ። ሆኖም ግልፅ ነው በክፍለ ዓለማችን ሴቶች አሁንም ቢሆን ነፃ እንዳልሆኑ አልረሳም »

ለብዙ አፍሪቃውያት አርአያ የሆኑት የ63 ዓመቷ ድላማኒ ዙማ በተፎካካሪዎቻቸውም ዘንድ አልፎ አልፎ ንቅንቅ የማይል ፅኑ አቋም እንዳላቸው ዓላማቸውን ለማራመድ ወሳኝ እርምጃ በመወስድ ነው የሚታወቁት ። በተፈጥሮአቸውው ታጋይ ናቸው ። አስቀድሞም የፖለቲካ ዝንባሌ የነበራቸው ድላማኒ በለጋ እድሚያቸው የደቡብ አፍሪቃው ብሔራዊ ምክር ቤት አባል ሆኑ ። በሃያ ዎቹ አጋማሽ እድሜያቸው ላይም የትውልድ አካባቢያቸውን የክዋዙሉ ናታልን ክፍለ ግዛት ለቀው ወደ ብሪታኒያ ተሰደዱ ። በብሪታኒያም ህክምና እየተማሩ ከትምህርቱ ጎን ለጎን በፀረ አፓርታይድ እንቅሳቃሴ ይሳተፉ ነበር ። እጎአ በ1982 ከአሁኑ የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዝዳንት ጄኮብ ዙማ ጋር ትዳር መስርተው 4 ልጆች አፍርተዋል ። ከ 16 ዓመታት በኋላ ፣ በ 1998 ከጄኮብ ዙማ ጋር ተለያዩ ። በማንዴላ ካቢኔ በጤና ሚኒስትርነት ጥሩ ስም ያተረፉት ድላማኒ ዙማ ከባለቤታቸው ጋር በተለያዩ በዓመቱ የመጀመሪያዋ ሴት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው ተሾሙ ።

ምስል picture-alliance/ dpa

በዚሁ ሃላፊነታቸው በኮንጎ ዲሞክራሲያዊት ሪፕብሊክ የሰላም ድርድር በሸምጋይነት ባደረጉት አስተዋጽኦ ይወደሳሉ ። ይሁንና የዚምባብዌ ፕሬዝዳንት ሮበርት ሙጋቤ ተግባራዊ ባደረጉትና በሺህዎች የሚቆጠሩ ነጭ ገበሬዎችን በኃይል ባፈናቀለው የመሬት ይዞታ ማሻሻያ ላይ አንዳችም ወቀሳ ባለመሰንዘር ይተቻሉ ። እጎአ በ2009 ጄኮብ ዙማ የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዝዳንት ሲሆኑ የቀድሞ ባለቤታቸው ድላማኒ ዙማ የሃገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ሆኑ ። በአዲሱ ሃላፊነታቸውም ከከፍተኛ ሥልጣን ዝቅ እንደተደረጉ ነበር የፖለቲካ ታዛቢዎች አስተያየታቸውን የሰጡት ። ድላማኒ ዙማ ግን ሃላፊነቱን እንደወሰዱ የመስሪያ ቤቱን ያልጸዳ አሰራር ማስተካከል ላይ ነበር ያተኮሩት ። « ሙሰኛ ባለሥልጣናት ከክፍሉ መሰናበት አለባቸው ። በማንኛውም ደረጃ ቢሆን ሙሰኛ ባለሥልጣንን ቸል ልንል አይገባም ። ሁላችንም ታማኝ መሆን አለብን ፤ ሥራችንንም በታማኝነት ማከናወን ይገባናል ።»

ድላማኒ ዙማ ከቀድሞው የጀርመን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሽታይንማየር ጋርምስል picture-alliance/ dpa

ድላማኒ ዙማ ያሉትን በተግባር የሚተረጉሙ መሆናቸውን በተለያዩ ጊዜያት አስመስክረዋል ። የሃገር አስተዳደር ሚኒስቴር በታሪኩ የሂሳብ መርማሪዎች ጥፋት ያላገኙበት በርሳቸው የሥልጣን ዘመን ነው ። ለአዲሱ ሃላፊነታቸውም የፖለቲካ ተሞክሮአቸው ፣ የማያወላውል አቋማቸውን ፣ ዲፕሎማሲ ክህሎታቸው ጠቃሚ ነው ። እንደ አፍሪቃ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበርነታቸው የተሰነጣጠረውን የአባል መንግሥታቱ አቋም አሰተባብረው ድርጅቱ አንድ አቋም እንዲይዝና በዛ ያሉት የክፍለ ዓለሙን አንገብጋቢ ችግሮች መፍትሄ ያገኙ ዘንድ የተላለፉ ውሳኔዎች ተገባራዊ እንዲሆኑ ማብቃት ይጠበቅባቸዋል ። ለእነዚህ ተግዳሮቶች መፍትሄ ለመሻት ወይዘሮ ድላማኒ ዙማ ብቃቱ እንዳላቸው ደቡብ አፍሪቃውያን ይተማመኑባቸዋል ።

ሂሩት መለሰ

ነጋሽ መሐመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW