አሳሳቢዉ ጦርነቱና የአዲስ አበባ ወሰን ጉዳይ
ዓርብ፣ ነሐሴ 20 2014
የትግራይ ሕዝብ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አሸባሪ ተብሎ ለተፈረጀው ሕወሓት ሊተው አይገባም ሲሉ ሦስት የፖለቲካ ፓርቲዎች በጋራ በሰጡት መግለጫ ተናገሩ። ፓርቲዎቹ ዳግም ከሰሞኑ የተቀሰቀሰው ጦርነት በሰላም እንዲፈታ ሁሉም ወገኖች እስከመጨረሻው ጥረት እንዲያደርጉም ጠይቀዋል። የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)፣ እናት እና የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) የተባሉት ሦስት የፖለቲካ ፓርቲዎች ዛሬ በጋራ በሰጡት መግለጫ «በአዲስ አበባ ከተማ እና በኦሮሚያ ክልል መካከል የተደረገው የወሰን ማካለል ተግባር በአስቸኳይ እንዲቆም» ሲሉም ድርጊቱ ሕገ ወጥ መሆኑን ጠቅሰው ጠይቀዋል።
መኢአድ ፣ እናት እና ኢሕአፓ ፓርቲዎች በፌዴራል መንግሥት እና በሕወሓት መካከል የተጀመረው ዳግም ግጭት አሁንም በሰላም አማራጮች እንዲፈታ ጠይቀዋል። ከእናት ፓርቲ በመጋቢ ሀዲስ ሳሙኤል በንባብ የቀረበው መግለጫ «የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ክልልን ወሰን የማካለሉ ሥራ ከሕግ ውጪ የተደረገ ነው» ይላል። በከተማዋ መታወቂያ ከሕግ ውጪ ይታደላል፣ ዘረፋ በከፋ ሁኔታ ቀጥሏል፣ ታሪካዊ ቅርሶችም በማናለብኝነት ይፈርሳሉ፣ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ደግሞ ያለአግባብ ለማይገባው ይታደላሉ ብሏል።
ፓርቲዎቹ የወሰን ማካለሉ ጉዳይ በብሔራዊ ምክክሩ አንድ ጉዳይ ሆኖ መፈታት ሲገባው በይድረስ ይድረስ መሠራቱ ወደፊት ብዙ በከተማዋ ውስጥ የነበረን ሕዝብን ለአስተዳደራዊ ችግር ያጋልጣል ብለዋል። ይህንኑ ጉዳይ በተመለከተ ከወጣቶች ጋር ከሰሞኑ በተወያዩበት ወቅት ምላሽ የሰጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የማካለሉ ተግባር ፓርቲያቸው «ብልጽግና ከሠራቸው ማንኛውም ሥራ የላቀውና ትልቁ ነው» ብለዋል።
ሰለሞን ሙጬ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ሸዋዬ ለገሰ