እንወያይ፤ አሳሳቢው በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ መራቅ
እሑድ፣ ሚያዝያ 26 2017
በቅርቡ በባህር ዳር ከተማ በተካሄደ ስብሰባ የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሀኑ ነጋ እንዳሉት በግጭቶችና በሌሎችም ምክንያቶች በመላ አገሪቱ መማር ከነበረባቸው ህትጻናትና ታዳጊዎች መካከል 7.8 ሚሊዮን የሚሆኑት ከትምህርት ውጪ ሆነዋል። ከነዚህም መካከል 4 ሚሊዮን ያክሉ በአማራ ክልል መሆናቸው ተገልጿል። ፕሮፌሰር ብርሀኑ ሰሞኑን በተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡት ሪፖርትም በግጭቶችና በሌሎች ምክንያቶች በመላ አገሪቱ 8 ሚሊዮን የሚሆኑ ተማሪዎች ከትምህርት ውጪ መሆናቸውን በድጋሚ ገልጸዋል።
በትግራይ ክልልም 1 ነጥብ 2 ሚልዮን ህፃናት እና ታዳጊዎች ወደ ትምህርት ገበታ አለመመለሳቸው የክልሉ ትምህርት ቢሮ በቅርቡ አስታውቋል። በክልሉ 60 ከመቶ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው ያልተመለሱ ሲሆን፤ በትምህርት ጥራት እና ተደራሽነት ላይ ሰፊ ክፍተት እየተስተዋለ መሆኑም ቢሮው ገልጿል።
የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ በበኩሉ በበጀት ዓምቱ 7 ሚሊዮን ተማሪዎችን ለመመዝገብ ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፤ ባለፉት 8 ወራት ለ3 ጊዜ ያክል የተማሪዎች ምዝገባ ለማድረግ ተሞክሮ የተመዘገቡ ተማሪዎች ቁጥር አሁንም ከታቀደው ከግማሽ በታች መሆኑን ገልጿል፡፡
ምንም እንኳ ቁጥሩን የትምህርት ሚንስቴር ባይቀበለውም የተባበሩት መንግሥታት የሕጻናት መርጃ ድርጅት (UNICEF) በታኅሳስ 2017 ባወጣው መረጃም ከዘጠኝ ሚሊዮን በላይ የኢትዮጵያ ልጆች በሰው ሠራሽ እና የተፈጥሮ አደጋዎች ከትምህርት ቤት ውጪ መሆናቸውን ይፋ አድርጓል። በሪፖርቱ መሠረት በአማራ ክልል 4.4 ሚሊዮን፣ በኦሮሚያ ክልል 3.2 ሚሊዮን፤ በትግራይ ክልል 1.2 ሚሊዮን ልጆች ትምህርት ቤት አይሔዱም።ግጭት፣ ብጥብጥ፣ የተፈጥሮ አደጋዎች እና መፈናቀል ልጆችን ከትምህርት ያራቁ ዋንኛ ምክንያቶች ሆነው ተጠቅሰዋል።
በዚህ የተናሳ በርካታ አዳጊ ወጣቶች ለህገ ወጥ ስደት በአንዳንድ አካባቢዎች ደግሞ ወጣት ልጃገረዶች ለያለእድሜ ጋብቻ እየተዳረጉመሆኑ ይነገራል።
በዚህ መልኩ የተማሪዎች ከትምህርት ገበታ መራቅ የሚያስከትለው ጉዳት ምን ይመስላል? ለወደፊቱስ በግለሰብ ፣በኅብረተሰብ እና በሀገሪቱ የሚያመጣው ሁለንተናዊ ችግርስ? እንደ መፍትሄ ምንስ መደረግ አለበት ?አሳሳቢው በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ መራቅ የዚህ ሳምንት የእንወያይ ዝግጅት ማጠንጠኛ ነው።
በውይይቱ ሶስት እንግዶች ተሳትፈዋል።
1,አቶ ማሞ መገሻ አንጋፋ የትምህርት ባለሙያ
2, ፕሮፌሰር ሃምቤሳ ቀንዓ ከፍተኛ የትምህርት ባለሙያ እና ከአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ
3, ዶክተር አብርሃ ኪሮስ የትምህርት ባለሙያ እና በዘርፉ ጥናት ያደረጉ ናቸው።
ሙሉ ውይይቱን የድምፅ ማዕቀፉን ተጭነው እንዲያደምጡ እንጋብዛለን።
ፀሀይ ጫኔ