አንድ ዓመት ከአሜሪካና አፍሪቃ መሪዎች ጉባኤ ወዲህ
ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 4 2016
ዩናይትድ ስቴትስ ለአፍሪቃ አኅጉር የገባችውን ቃልኪዳን በመፈጸም ረገድ ባለፈው አንድ ዓመት ከፍተኛ ዕድገት ማሳየቷ ተገለጸ ። የአሜሪካ አፍሪቃ መሪዎች ጉባዔ አንደኛ ዓመትን አስመልክቶ በተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ፣ ዩናይትድ ስቴትስ በንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ በፀጥታና መልካም አስተዳደር ለአፍሪቃ አኅጉር የምትሰጠው ድጋፍና ትኩረት እየተጠናከረ ነው ።
የአፍሪቃ አሜሪካ መሪዎች ጉባዔ ውሳኔዎች አተገባበር
በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ አምና የተካሄደውና ስኬታማ የተባለው፣ የዩናይትድ ስቴትስና የአፍሪቃ መሪዎች ጉባዔ ውሳኔዎች አተገባበር ላይ ታይተዋል የተባሉ ዕድገት ተዳሰዋል።
እንዲሁም፣ እነዚህን ጥረቶች መሠረት በማድረግ አሜሪካ አፍሪቃን ለማገዝ ያላትን ቁርጠኝነት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባለሥልጣናት አጉልተው አስምተዋል።
በአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት የብሔራዊ ደህንነት የአፍሪቃ ጉዳዮች ከፍተኛ ዳይሬክተር ጁድ ዴቨርመንት እንደሚሉት፣ የባይደን አስተዳደር በጉባዔው ላይ በሦስት ዓመታት ውስጥ፣ ለአፍሪቃ አኅጉር 55 ቢሊዮን ዶላር ስምምነት ለመፈጸም በገባው ቃል መሠረት፦ እስካሁን 40 በመቶውን ተግብሯል።
በሁለተኛው ዓመት ላይ ደግሞ፣ሰባ ከመቶ ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል
በዚህ መዋዕለ ንዋይ፣ አሜሪካከአፍሪቃ ጋር ያላትን የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር ማስፋፋት እንደቻለች እኚሁ ዳይሬክተር ዐስታውቀዋል። እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ፦ በአንድ ነጥብ ሁለት ቢሊዮን ዶላር፣ የአሜሪካን የውጭ ንግድ ለፀሃይ ፕሮጀክቶች፣ በአንጎላ ድልድይ መሠረተ ልማት እና በኢትዮጵያ የንግድ አውሮፕላኖች ድጋፍ ይካትታሉ።
በመጪው የ2024 የጎርጎሮሳዊው አዲስ ዓመት፣ከ ዚህ መጠን በእጥፍ የሚበልጥ ጠንካራ ስራዎች እንደሚቀጥሉ ሚስተር ዴቨርመንት ጠቁመዋል። አዲስ የጸጥታና የመልካም አስተዳደር ትብብር መፈጠሩን አንዲሁም በዲያስፖራ የተደገፈ የሕዝብ ተሳትፎ እንዲጠናከር መደረጉንም አብራርተዋል።
አፍሪቃ በዓለም መድረክ
ሚስተር ዴቨርመንት፣አፍሪቃ በዓለም መድረክ ያላት ተሣትፎ እንዲጠናከር አሜሪካ የምታደርገውን ድጋፍ ሲገለጹ የሚከተለውን ብለዋል። "ፕሬዚዳንት ባይደን፣ዓለም አቀፍ ተግዳሮቶች ተነስተው ውይይት በሚደረግባቸው መድረኮች እና ውሳኔዎች በሚተላለፍባቸው ተቋሞች ሁሉ የአፍሪቃ ድምጽ ሊካተት እንደሚገባ ግልጽ አድርገዋል። እንደምስታውሱት ፣ባለፈው ዓመት የአፍሪቃ ህብረት የቡድን ሃያ ቋሚ አባል እንዲሆን ጥሪ አቅርበው ነበር። ይኸው ጉዳይ ባለፈው መስከረም ወር ተፈጻሚ ሆኖ በደስታ ተቀብለነዋል። አሁን ደግሞ ከሠዓራ በታች ያሉ ሃገሮች በዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት ቦርድ ውስጥ፣መቀመጫ እንዲኖራቸው እየደገፍን ነው።"
በተጨማሪም በተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ምክር ቤት አፍሪቃ ቋሚ ውክልና እንድታገኝ፣አሜሪካ ጥሪ እያሰማች መሆኑን ዳይሬክተሩ ተናግረዋል። አሜሪካ ከአፍሪቃ ሃገሮች ጋር ያላትን ግንኙን የበለጠ ለማጠናከር በከፍተኛ ባለስልጣኖቿ አማካይነት ስፍር ቁጥር የሌላቸው ጉብኝቶች ወደ አህጉሪቱ መካሄደቸውን የተናገሩት ሚስተር ዴቨርመንት፣ፕሬዚዳንት ጆሴፍ ባይደንም ጉብኝቱን ለማካሄድ ቁርጠኛ አቋም እንዳላቸው ጠቁመዋል።
በአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት የአፍሪቃ ጉዳዮች ቢሮ ረዳት ጸሐፊ ጆናታን ፕራት በበኩላቸው፣ በአሜሪካ አፍሪቃ መሪዎች ጉባዔወዲህ ውይይት የተደረገባቸውን ጉዳዮች ለመተግበር የተኼደውን ርቀት አመላክተዋል።
"የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ኃላፊው አንቶኒ ብሊንከን እና ሌሎች ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ወደ አፍሪቃ በመመላለስ በአህጉሪቱ የምግብ ዋስትና፣መልካም አስተዳደር፣ ምጣኔ ኃብት ልማትና በሌሎች አንገብጋቢ ጉዳዮች ላይ ትኩረት በመስጠት መክረዋል።”
አፍሪቃ ስትበለጽግ አሜሪካም ትበለጽጋለች
"አፍሪቃን እናበልጽግ" የተባለው ፕሮጀክት ዳይሬክተር ብሪቲሽ ሮቢንሰን በፈንታቸው፣በጣም አስፈላጊ እና እያደገች ያለች ያሏት አፍሪቃ፣በዓለም ላይ ለሚከሰቱ ታላላቅ ተግዳሮቶች መፍትሔ ለማፈላለግ ያላትን ወሳኝ ሚና አስመልክተው ማብራሪያ ሰጥተዋል። ሚስ ሮቢንሰን፣የአሜሪካ ብልጽግና ከአፍሪቃ ዕድገት ጋር የተሳሰረ እንደሆነም አመልክተዋል። ዳይሬክተሩ፣አፍሪቃ ስትበለጽግ አሜሪካም ትበለጽጋለች ይላሉ። "አፍሪቃ የዓለምን የብዝሀ ሕይወት ሀብት ለመጠበቅ ግንባር ቀደም አህጉር ነች። የአሜሪካ ብልፅግና ከአፍሪቃ ዕድገት ጋር የተያያዘ ነው።"
አሜሪካ አሁን ወደ አፍሪቃ ትኩረቷን ያደረገችው፣በአህጉሪቱ እያደገ ያለውን የቻይና እና ሩሲያን ተጽእኖ ለመገዳደር ነው ሲሉ አስተያየት የሚሰጡ ታዛቢዎች አሉ።
ታሪኩ ኃይሉ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ሸዋዬ ለገሰ