አዲስ ተሿሚዋ የጀርመን መከላከያ ሚ/ር
ረቡዕ፣ ሐምሌ 10 2011ማስታወቂያ
ወይዘሮ አነግሬት ክራምፕ ካረንባወር ዛሬ በይፋ የጀርመን መከላከያ ሚኒስትር ሆነው ተሰየሙ። ካረንባወር ሹመቱ የተሰጣቸው ትናንት የአውሮጳ ህብረት የህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት የጀርመን መከላከያ ሚኒስትር ኡርዙላ ፎን ዴር ላየንን የህብረቱ ኮሚሽን ፕሬዝዳንት አድርጎ ከመረጠ በኋላ ነበር። ለካረንባወር ዛሬ የሹመት ደብዳቤያቸውን የሰጧቸው በእረፍት ላይ የሚገኙትን የጀርመን ፕሬዝዳንት ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየርን የተኩት የበርሊን ከንቲባ ሚሻዜል ሙለር ናቸው። በዚሁ ወቅት ባሰሙት ንግግርም ካረንባወር የጀርመንን ደህንነት በማስከበር ረገድ ከባድ ሃላፊነት የተጣለበትን መሥሪያ ቤት ሃላፊነት ተረክበዋል ብለዋል። በዚሁ ሥነ-ስርዓት ላይ መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል እና ፎን ዴር ላየን ተገኝተዋል። ካረንባወር በወቅቱ ባሰሙት ንግግር በወታደሮች ደህንነት ላይ ይበልጥ ለማተኮር ቃል ገብተዋል። የጀርመን ክርስቲያን ዴሞክራት ፓርቲ ሊቀመንበር ወይዘሮ ካረንባወር የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችን ኃላፊነት ከመውሰድ ይልቅ በፓርቲያቸው ጉዳይ ላይ ይበልጥ ማተኮር እንደሚፈልጉ ከዚህ ቀደም ተናግረው ስለነበረ የመከላከያ ሚኒስትርነት ሃላፊነትን መቀበላቸው አስገርሟል።
ኂሩት መለሰ
አዜብ ታደሰ