ኢትዮጵያዉያን አትሌቶች በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የማጣሪያ ውድድሮችን አለፉ
ቅዳሜ፣ መስከረም 3 2018
ዛሬ በተጀመረው የጃፓን ቶኪዮ 20ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያዉያን አትሌቶች በማጣሪያ ውድድሮች ወደ ቀጣዩ ዙር ማለፋቸውን አረጋግጠዋል። በሴቶች የ1500 ሜትር የማጣሪያ ውድድር የተካፈለችው አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ ከምድቧ አንደኛ በመውጣት ወደ ግማሽ ፍጻሜ ማለፏን አረጋግጣለች ።
በውድድሩ በምድብ አንድ ውስጥ የተሳተፈችው አትሌት ሳሮን በርሄ 9ኛ በመውጣት ወደ ቀጣዩ ዙር ማለፍ ሳትችል ቀርታለች። ኢትዮጵያን በመወከል በ1500 ሜትር ጥሩ ሰዓት የነበራት አትሌት ድርቤ ወልተጂ ከጸረ አበረታች መድሃኒት ምርመራ ጋር በተያያዘ በውድድሩ እንዳትካፈል ዉሳኔ መተላለፉ ተነግሯል። ነገ እሁድ ከሰዓት በኋላ 9:15 ላይ የግማሽ ፍጻሜ ውድድር እንደሚደረግ ይጠበቃል። በውድድሩ ኬንያዊቷ ፌዝ ኪፒገን ለፍሬወይኒ ብርቱ ተፎካካሪ እንደምትሆን ይጠበቃል።
ቀደም ብሎ በተደረገው የወንዶች የ3000 ሜትር መሰናክል የማጣሪያ ውድድር ሶስቱም አትሌቶች ለፍጻሜ ማለፋቸውን አረጋግጠዋል። ለፍጻሜ ተፋላሚነታቸውን ያረጋገጡት አትሌት ለሜቻ ግርማ ፣ ሳሙኤል ፍሬው እና ጌትነት ዋለ ከሞሮኮው አትሌቶች ሱፍያን ኤል ባካሊ እና ሳላዲኔ ቤን ያዚዴ እንዲሁም ኒውዚላንዳዊ ጆርዴ ባሚሽ ብርቱ ፉክክር ይጠብቃቸዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከደቂቃዎች በኋላ የሚደረገው የሴቶች የ10,000 ሜትር የሩጫ ውድድር ኢትዮጵያ የመጀመሪያ ሜዳሊያዋን ልታገኝ ትችላለች የሚል ግምት ተሰጥቷታል። በውድድሩ ተሳታፊ የሚሆኑት ጉዳፍ ጸጋይ ፣ ጽጌ ገብረ ሰላማ ፣ እጅጋየሁ ታዬ ፣ ፉቴይን ተስፋይ ከኬንያ ፣ ዩጋንዳ እና ብሪታንያ አትሌቶች ጋር በተመሳሳይ ብርቱ ፍክክር ይጠብቃቸዋል።