1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

ኢትዮጵያ እና ኤርትራ “ማንኛውንም ውጥረት በዲፕሎማሲያዊ መንገድ እንዲፈቱ” ሀገራት ጥሪ አቀረቡ

ቅዳሜ፣ ታኅሣሥ 4 2018

ኢትዮጵያ እና ኤርትራ “ማንኛውንም ውጥረት ወይም አለመግባባት በሰላማዊ እና በዲፕሎማሲያዊ መንገድ እንዲፈቱ” የአውሮፓ ኅብረት እና ብሪታኒያን ጨምሮ ሀገራት ጥሪ አቀረቡ። ሀገራቱ የአልጀርስ ሥምምነትን 25ኛ ዓመት እያስታከኩ ያወጧቸው መግለጫዎች በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል ያለው ውጥረት እንዳሳሰባቸው የሚጠቁሙ ናቸው።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና ፕሬዝደንት ኢሳያስ አፈወርቂ በኢትዮጵያ
በ1993 በአልጀርስ እንዲሁም በ2010 በአስመራ በተፈረሙት ሥምምነቶች መሠረት ኢትዮጵያ እና ኤርትራ አንዳቸው የሌላቸውን “ሉዓላዊነት፣ ነጻነት እና የግዛት አንድነት” እንዲያከብሩ የአውሮፓ ኅብረት ጥሪ አቅርቧል።ምስል፦ Reuters/T. Negeri

ኢትዮጵያ እና የኤርትራ “ሉዓላዊነት፣ ነጻነት እና የግዛት አንድነት እንዲከበር” ብሪታኒያ እና ቱርክን ጨምሮ አምስት ሀገራት በጋራ ጥሪ አቀረቡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና ፕሬዝደንት ኢሳያስ አፈወርቂ በሐምሌ 2010 በተፈራረሙት “የሰላም ሥምምነት መንፈስ ማንኛውም ውጥረት ወይም አለመግባባት በሰላም እና በዲፕሎማሲያዊ መንገድ እንዲፈታ” ጠይቀዋል። 

የካናዳ፣ ጃፓን፣ ኖርዌይ፣ ቱርክ እና ዩናይትድ ኪንግደም መንግሥታት ጥሪውን ያቀረቡት የአልጀርስ ሥምምነት የተፈረመበትን 25ኛ ዓመት በማስመልከት ትላንት አርብ ባወጡት መግለጫ ነው። 

ሀገራቱ በ1993 የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እና ፕሬዝደንት ኢሳያስ አፈወርቂ በአልጀርስ የተፈራረሙትን ሥምምነት፣ ሥምምነቱ የሚያራምዳቸውን መርኆዎች እና በሥምምነቱ የተቋቋመው ኮሚሽን የወሰናቸውን ድንበሮች እንደሚደግፉ በጋራ መግለጫቸው ጠቁመዋል።

የአውሮፓ ኅብረት “የአልጀርስ ሥምምነትን እና በድንበር ኮሚሽኑ የተወሰነውን” የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ድንበር “ሙሉ በሙሉ” እንደሚደግፍ አስታውቋል።

በ1993 በአልጀርስ እንዲሁም በ2010 በአስመራ በተፈረሙት ሥምምነቶች መሠረት ኢትዮጵያ እና ኤርትራ አንዳቸው የሌላቸውን “ሉዓላዊነት፣ ነጻነት እና የግዛት አንድነት” እንዲያከብሩ የአውሮፓ ኅብረት ጥሪ አቅርቧል።

ኅብረቱ እንደሚለው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እና ፕሬዝደንት ኢሳያስ የአስመራ መግለጫን ሲፈራረሙ “ሁለቱ ሀገሮች የአልጀርስ ሥምምነትን እና በሥምምነቱ በተቋቋመው የድንበር ኮሚሽን የተወሰነውን ድንበር ለማክበር ያላቸውን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል።” 

ሁለቱም ወገኖች “ማንኛውንም ውጥረት ወይም አለመግባባት በሰላማዊ እና በዲፕሎማሲያዊ መንገድ እንዲፈቱ” ጥሪ ያቀረበው የአውሮፓ ኅብረት “ይህ ለቀጠናው መረጋጋት ቁልፍ” እንደሆነ አሳስቧል። 

ሀገራቱ የአልጀርስ ሥምምነትን እያስታከኩ ያወጧቸው መግለጫዎችበኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል ያለው ውጥረት እንዳሳሰባቸው የሚጠቁሙ ናቸው።

የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሀፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ኢትዮጵያ እና ኤርትራ “ለዘላቂ ሰላም” እና አንዳቸው የሌላውን “ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት” ለማክበር ለተፈራረሙት የአልጀርስ ሥምምነት ቁርጠኝነታቸውን እንዲያረጋግጡ ትላንት አርብ ጥሪ አቅርበው ነበር። 

አርታዒ ታምራት ዲንሳ 
 

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW