እንወያይ፤ ኢትዮጵያ ባለፉት 50 ዓመታት ወደ ተሻለ የፖለቲካ ምህዳር ለምን መሻገር አቃታት?
እሑድ፣ መጋቢት 21 2017
በኢትዮጵያ በ1966 ዓ.ም በተነሳው አብዮት የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሳዊ አገዛዝ አብቅቷል። ይህንን ተከትሎ በመጋቢት 19 67 ዓ/ም የዛሬ 50 ዓመት ገደማ ደርግ፤ዘውዳዊውን ስርአት በአዋጅ በማስወገድ ማርክሲዝም-ሌኒኒዝምን የሀገሪቱ የፖለቲካ መመሪያ እና ርዕዮተ ዓለም በማድረግ ስልጣኑን አደላድሏል።
በሌላ በኩል ለአፄ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት ውድቀት ወሳኝ የነበረው እና «መሬት ላራሹ» የሚል መፈክር አንግቦ የተነሳው የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ፤ ዓላማው በጊዜው የነበረውን ዘውዳዊ ስርዓት በማስወገድ ወደ ግራ ያዘነበለ እና የተሻለ የሚሉትን ሶሻሊስታዊ ስርዓት ለማምጣት እንደነበረ በብዙዎች ይነገራል።ያም ሆኖ ውጤቱ በታሰበው መንገድ ሳይሆን፤ ብዙ ደም መፋሰስን እና እንደ ደርግ ያለ አምባገነን ስርዓትን አምጥቷል።
ከ17 ዓመታት የእርስ በእርስ ጦርነት በኋላ ደርግን ከስልጣን አስወግዶ ወደ ስልጣን በመጣው ኢህአዴግም በሀገሪቱ አንፃራዊ ሰላም እና ኢኮኖሚ እድገት ታይቷል ቢባልም፤ የፖለቲካ ምህዳሩ ግን ለመነጋገር እና ለመወያየት ቦታ የሚሰጥ አልነበረም።
ከድህረ ኢህአዲግበኋላም በቅርቡ የፖለቲካ ችግር የወለደው የእርስበርስ ጦርነት፤ በብዙ መቶ ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ህይዎታቸውን አጥተዋል።ከፍተኛ የንብረት ውድመት እንዲሁም የሰብዓዊ መብት ጥሰት አስከትሏል። በዚህ ሁኔታ በኢትዮጵያ መንግስታት ቢቀያየሩም ከ50 ዓመታት በኋላ እንኳ በሀገሪቱ ብዙ ያልተፈቱ የፖለቲካ ችግሮች እንዳሉ በብዙዎች ዘንድ ተደጋግሞ ይነሳል።
ለመሆኑ ኢትዮጵያ ወደ ተሻለ ሰላም ሀገራዊ አንድነት እና የፖለቲካ ምህዳር ለምን መሻገር አቃታት?ከዚህ አዙሪትስ እንዴት መውጣት ይቻላል? የዚህ ሳምንት የእንወያይ ዝግጅታችን ማጠንጠኛ ነው።
በውይይቱ አራት እንግዶች ተሳትፈዋል።
1, ልዑል ዶ/ር አስፋ ወሰን አስራተ...........በጀርመን የአፍሪቃ እና የመካከለኛዉ ምስራቅ ጉዳዮች አማካሪ፤ እንዲሁም የታሪክ ምሁሩ እና ፀሀፊ ናቸው።
2, አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ............አንጋፋ ፖለቲከኛ እና ደራሲ
3, ዶክተር ዮናስ አሽኔ ................. በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ የፖለቲካ እና የዓለም አቀፍ ግኑኝነት ትምህርት ክፍል መምህር
4, በፈቃዱ ሀይሉ........ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች
ሙሉ ውይይቱን የድምፅ ማዕቀፉን ተጭነው እንዲያደምጡ እንጋብዛለን።
ፀሐይ ጫኔ