ኢትዮጵያ የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ም/ ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሆና መመረጥዋ
ማክሰኞ፣ ኅዳር 30 2018
ኢትዮጵያ ለመጭዉ የጎርጎረሳዉያን 2026 ዓመት የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሆና ተመረጠች። ጄኔቫ ስዊዘርላንድ የሚገኘዉ የመንግስታቱ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ኢትዮያን መመረጥዋን ያሳወቀዉ ሰኞ ኅዳር 29 ፤ 2018 ባወጣዉ መግለጫ ነዉ።
ኢትዮጵያ የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ም/ ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሆና መመረጥዋ
ኢትዮጵያ ለመጭዉ የጎርጎረሳዉያን 2026 ዓመት የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሆና ተመረጠች። ከኢትዮጵያ ሌላ ኢስቶኒያ እና ስፔን በየክልላቸዉ በመጭዉ 2026 የጎርጎረሳዉያን ዓመት የመንግሥታቱ ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት በምክትል ፕሬዚዳንት ሆነዉ እንዲያገለግሉ ተመርጠዋል።
ጄኔቫ ስዊዘርላንድ የሚገኘዉ የመንግሥታቱ ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት ትናንት ጥር 29 ቀን 2018 ዓ.ም ይፋ ባደረገዉ መግለጫ፤ በጄኔቫ ለሚገኘዉ ቢሮ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነዉ እንዲያገለግሉ ሦስት አምባሳደሮችን መርጧል። በምክትል ፕሬዚዳነትነት የሚያገለግሉት ቦታዉ ላይ የሚገኙት የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ፀጋብ ከበበው ዳካ - የአፍሪቃ መንግስታት ቡድንን በመወከል፣ የኢስቶኒያዋ ሪያ ሳልሳ-ኦዲፍረን የምስራቃዊ አውሮጳ መንግስታት ቡድንን እንዲሁም የስፔኑ ማርኮስ ጎሜዝ ማርቲኔዝ የምዕራብ አውሮጳ ሀገራት ቡድንን በመወከል በምክትል ፕሬዚዳንትነት ተሰይመዋል። የኢትዮጵያን የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሆና ተመረጠች ማለት ምን ማለት ነዉ ስንል የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ሆነዉ ያገለገሉትን፤ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች አቶ ያሬድ ኃይለማርያምን ጠይቀናቸዋል።
ምክር ቤቱ በየዓመቱ ይመርጣል
«መቀመጫዉን ጄኔቫ ስዊዘርላንድ ያደረገዉ፤ የመንግሥታቱ ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት፤ አምስት ምክትል ፕሬዚዳንት እና አንድ ዋና ፕሬዚደንት በየዓመቱ ይመረጣሉ። ምክትል ፕሬዚዳቱቹ በተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት፤ መላዉን ዓለም የሚወክሉ 48 ሃገራት ፤ በየክልላቸዉ ወይም በአህጉራዊ ማዕቀፉ፤ የተካለሉ ናቸዉ። የአፍሪቃ ቡድን፤ የአረብ ሃገሮች ቡድን፤ የላቲን አሜሪካ ቡድን፤ የምዕራብ እና የምስራቅ አዉሮጳ ቡድን ተብሎ የተደለደለ ነዉ። በአምስት ቡድን ዉስጥ ያሉት እነዚህ የአገሮች ስብስብ ፤ በአንዳንድ ሰዉ ይወከላሉ። ይህ ምርጫ ሁሉም አባል ሃገራት በዙር የሚደርሳቸዉ ጉዳይ ነዉ። እናም ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነዉ የተመረጡት የቡድን ተወካዮች ትልቁ ስራቸዉ ዋናዋን ፕሬዚዳንት ማገዝ፤ መደገፍ ስብሰባዎችን መምራት ፤ አንዳንድ የሚደረጉ ግንኙነቶች ላይ መረጃ መቀበል፤ መስጠት ነዉ። በምክትል ፕሬዚደንትነት መመረጥ ማለት ከሃገሮቹ የሰብዓዊ መብት አያያዝ ጋር ተያያዝ ነዉ ማለት አይደለም። ፤ በሰብዓዊ በብቶች ምን አይነት መጥፎ ሃገር ይሁን፤ ጥሩ ሃገር ይሁን ከዝያ ጋር የሚያይዘ ዉ ነገር የለም።»
የመንግሥታቱ ድርጅት ይፋ ባደረገዉ መግለጫ ቆየት ብሎ የላቲን አሜሪካ እና የካሪቢያን ግዛቶች ቡድን አራተኛ ምክትል ፕሬዚዳንት እንዲሁም ከእስያ -ፓሲፊክ መንግሥታት ቡድን ፕሬዚዳንት ሆኖ እንደሚሾም በመግለጫዉ ጠቁሟል።
«ትልቁ ነገር ኢትዮጵያ እንደዚሁ ለሁለት ዓመት ተመርጣ በሌሎች ቦታዎች ላይም አገልግላለች። ይሄ ምርጫ ለሃገሮች የበለጠ ጫና ነዉ የሚፈጥረዉ። በሰብዓዊ መብት ላይ በዓለም አአፍ ደረጃ እንዲህ አይነት ቦታን ስትይዙ ፤ የሃገራችሁን የሰብዓዊ መብት ሁኔታ በመጠበቅ ረገድ ፤ የበለጠ እዳ የሚጣልበት፤ መንገድ ነዉ ግን ፤ በጣም የተጋነነ በተለይ መንግሥት በሚቆጣጠራቸዉ ሚዲያዎች በተራገበዉ መንገድ ፤ ኢትዮጵያ በሰብዓዊ መብት አያያዝ ፤ ተመስግና ፤ ወይም ለዝያ የተደረገ እዉቅና አይነት፤ የስልጣን መያዝ ፤ ተደርጎ የሚዘገብበት መንገድ ፤ በጣም የተሳሳተ እና ልክም አይደለም።»
42 ሃገራት ለኮሚሽኑ የላኩት ደብዳቤ
አቶ ያሬድ በቅርቡ 42 የአዉሮጳ ሃገራት ለዚሁ ጄኔቫ ለሚገኘዉ የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ደብዳቤ አስገብተዉ ነበር? « 42 ቱ ሃገሮች ያወጡት መግለጫ፤ ኢትዮጵያ ዉስጥ ያለዉ በዋነኝነት፤ የሲቪክ ምህዳሩ ከእለት እለት በጣም እየጠበበ እና ለዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታም ይሁን ፤ በቀጣይ ምርጫዎችን በነፃነት ለማካሄድ፤ አመቺ እየሆነ አለመምጣቱ በጣም እንዳሳሰባቸዉ፤ ሲቢክ ማኅበራት ላይ የሚደርሰዉ ጫና ፤ ሃሳብን በመግለጽ መብት ላይ የሚደርሰዉ ጫና፤ ከዝያም አልፎ በሃገሪትዋ ዉስጥ እየተካሄደ ያሉ ግጭች እና ግጭቶቹ ንጹሐን ዜጎች ላይ እያደረሱ ያለዉ ጉዳት፤ የሃገሪቱን የሰብዓዊ መብት ሁኔታ ወደከፋ ደረጃ ላይ እያደረሰዉ ነዉ የሚል ጥልቅ ስጋት ያላቸዉ መሆኑን፤ እነዚህ ነገሮች በቶሎ ምላሽ ካልተሰጣቸዉ ፤ እንዲሻሻሉ ካልተደረገ ፤ የኢትዮጵያን ደረጃ ወደከፋ ሁኔታ ያደርሰዋል የሚል የጋራ መግለጫ ነዉ፤ መግለጫዉንም ያስገቡት ለተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ነዉ።»
አቶ ያሬድ ግን የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሆና ተመረጠች የሚለዉ ዜና መሬት ላይ ያለዉን ነገር ያላገናዘበ ነዉ ሲሉ ብዙዎች አስተያየቶችን ይሰማሉ። እዚህ ላይ የእርሶ አስተያየት ምንድን ነዉ ብለን ለጠየቅናወu አቶ ያሬድ፤ «ይሄ እንግዲህ በተለይ የኢትዮጵያ መንግሥት መገናኛ ብዙሃን ፤ ኅብረተሰቡን የሚያደናግሩባቸዉ ነገሮች ትንሽ ያሳስቡኛል። ይህ ከጋዜጠኝነት ስነምግባርም ያፈነገጠ ነዉ፤ ብለዋል። ኢትዮጵያ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት አባል ሆና በማገልገል ላይ የምትገኝ ሃገር መሆንዋ ይታወቃል።
አዜብ ታደሰ
ታምራት ዲንሳ