ኢትዮጵያ የአልጀርሱን ስምምነት ለመተግበር ወሰነች
ረቡዕ፣ ግንቦት 29 2010![Karte Äthiopien Eritrea Grenze Amharisch](https://static.dw.com/image/19357805_800.webp)
የኢትዮጵያ ገዢ ፓርቲ የኢሕአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የኢትዮጵያ እና የኤርትራን የድንበር ላይ ጦርነት ለማስቆም የሁለቱ ሐገራት መሪዎች በ1993 አልጀርስ-አልጄሪያ ላይ የተፈራረሙትን ሥምምነት ኢትዮጵያ ሙሉ በሙሉ መቀበሏን አስታዉቋል። ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴዉ ትናንት ባደረገዉ ስብሰባ በአልጀርሱ ሥምምነት መሠረት የተሰየመዉ የድንበር አካላይ ኮሚሽን ዉሳኔንምም ገቢራዊ ለማድረግ የኢትዮጵያ መንግሥት «ያለማመንታት በቁርጠኝነት» የሚሰራ መሆኑን ገልጧል። ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ከ1990 እስከ አልጀርሱ ስምምነት ለሁለት ዓመት ባደረጉት ጦርነት በመቶ ሺህ የሚቆጠር ሰው መሞቱ አይዘነጋም። የአልጀርሱ ስምምነት ቀጥታ ውጊያውን ቢያስቆምም ዘላቂ ሰላም ለማውረድ እስካሁን የጠቀመው ነገር የለም የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ መግለጫ እንደሚለው ኢትዮጵያ ስምምነቱን ሙሉ በሙሉ የተቀበለችው እና የድንበር አካላይ ኮሚሽኑን ውሳኔ ገቢር ለማድረግ የወሰነችው ሀያ ዓመት ያስቆጠረውን ፍጥጫ እና አለመተማመን ለማስወገድ ነው። የኢህአድግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ መንግሥት የሚቆጣጠራቸውን ትላልልቅ ኩባንያዎች እና ድርጅቶች በተወሰነ ደርጃ በአክስዮን ለግል ባለሀብቶች ለመሸጥ መታቀዱንም አስታውቋል። በሥራ አስፈጻሚው ኮሚቴ ውሳኔ መሠረት የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ኢትዮ ቴሌኮም፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይልን የመሳሰሉ ድርጅቶችን አብዛኛ ድርሻ መንግሥት ተቆጣጥሮ ቀሪውን ለሀገር ውስጥ እና ለውጭ ባለሀብቶች ለመሸጥ ታቅዷል። የመንግሥት ትላልቅ ተቋማትን ከፍተኛ ድርሻ መንግሥት ይዞ የተቀረዉን በአክሲዮን ለባለሐብቶች እንዲሸጥ ማቀዱ ተዘግቧልም።መንግሥት በሚቆጣጠራቸው ድርጅቶች የግል ባለሀብቶች እንዲሳተፉ የተፈለገው የሐገሪቱን የምጣኔ ሀብት እድገት ለማፋጠን ነው ተብሏል።
ነጋሽ መሐመድ
ኂሩት መለሰ