1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ
ፖለቲካኤርትራ

ኤርትራ ከኢጋድ ጥላ መውጣቷ እንዳሳዘናት የወቅቱ የኢጋድ ሊቀ-መንበር ጅቡቲ ገለጸች

ቅዳሜ፣ ታኅሣሥ 4 2018

ኤርትራ ከኢጋድ አባልነት ራሷን ለማግለል መወሰኗ እንዳሳዘናት የወቅቱ ሊቀ-መንበር ጅቡቲ ገለጸች። ኤርትራ ለሁለተኛ ጊዜ ጥላ ስትወጣ ኢጋድ “ለቀጠናው መረጋጋት ጉልህ አስተዋጽዖ ማበርከት” እንደተሳነው ተችታለች። ኤርትራ ክፍለ አኅጉራዊውን ድርጅት ከተቀላቀለችም በኋላ “በስብሰባዎች፣ ፕሮግራሞች ወይም እንቅስቃሴዎች” አለመሳተፏን ኢጋድ አስታውቋል።

ፕሬዝደንት ኢሳያስ አፈወርቂ
በፕሬዝደንት ኢሳያስ አፈወርቂ የሚመራው የኤርትራ መንግሥት ከምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግሥታት ድርጅት አባልነት ጥሎ ሲወጣ የአሁኑ ሁለተኛው ነው። ምስል፦ Stanislav Krasilnikov/TASS/AFP

ኤርትራ ከምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግሥታት ድርጅት አባልነት ራሷን ለማግለል ያሳለፈችው ውሳኔ እንዳሳዘናት የወቅቱ ኢጋድ ሊቀ-መንር ጅቡቲ አስታወቀች። የጅቡቲ የውጭ ጉዳይ እና ዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስቴር ዛሬ ቅዳሜ ባወጣው መግለጫ ጅቡቲ በሊቀ-መንበርነቷ እርምጃው ቢያሳዝናትም የኤርትራን “ሉዓላዊ ውሳኔ እንደምታከብር” ገልጿል። 

ኤርትራ ከክፍለ አኅጉራዊው ድርጅት ጥላ ስትወጣ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። ሀገሪቱ በጎርጎሮሳዊው 2003 ከድርጅቱ ከወጣች በኋላ ተመልሳ የተቀላቀለችው ከሁለት ዓመታት በፊት ነበር። ትላንት አርብ ከድርጅቱ አባልነት ጥላ ለመውጣት መወሰኗን ለኢጋድ ዋና ጸሀፊ ወርቅነህ ገበየሁ እንዳሳወቀች የኤርትራ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገልጿል።

ኢጋድ “በሕግ የተጣለበትን ኃላፊነት እና የተሰጠውን ሥልጣን” አጥቷል ያለው የኤርትራ ውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ለአባል ሀገራቱ “ምንም አይነት ስትራቴጂካዊ ጥቅም” መስጠት እንዳልቻለ እና “ለቀጠናው መረጋጋት ጉልህ አስተዋጽዖ ማበርከት” እንደተሳነው ተችቷል። 

የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግሥታት ድርጅት በበኩሉ ኤርትራ መልሳ ከተቀላቀለች በኋላም “በኢጋድ ስብሰባዎች፣ ፕሮግራሞች ወይም እንቅስቃሴዎች” አለመሳተፏን አስታውቋል። 

ኤርትራ ከኢጋድ አባልነት ለመውጣት የወሰነችው “ተጨባጭ ምክረ ሐሳቦች ሳታቀርብ፣ በተቋማዊ እና የፖሊሲ ማሻሻያዎች ላይ ተሳትፎ ሳታደርግ” መሆኑ “የሚያሳዝን” እንደሆነ ተችቷል። 

ኤርትራ ከኢጋድ ጥላ የወጣችው የክፍለ-አኅጉራዊው ድርጅት አባል ከሆነችው ጎረቤቷ ከኢትዮጵያ ጋር የተፈጠረው ፖለቲካዊ ውጥረት ባየለበት ወቅት ነው። ከኢትዮጵያ በተጨማሪ ጅቡቲ፣ ኬንያ፣ ሶማሊያ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሱዳን እና ዩጋንዳ የኢጋድ አባል ሀገራት ናቸው። 

አርታዒ ታምራት ዲንሳ 

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW