ከግማሽ የሚበልጠዉ የኢትዮጵያ ድንበር በቅጡ አልተከለም-ሚንስትር
ዓርብ፣ ሰኔ 6 2017
ኢትዮጵያ "ታሪክን፣ ሕግን እንዲሁም መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥን ታሳቢ ባደረገ ሁኔታ" የድንበር ማካለል ሥራን "ተቋማዊ ቅርጽ ሰጥታ" ለማከናወን በዝግጅት ላይ መሆኗን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታዉቋል።ኢትዮጵያን ከጎረቤቶቿ የሚያዋስናት "በሺዎች ኪሎ ሜትር የሚቆጠር ሰፊ ዓለም አቀፍ ድንበር" መኖሩን ሰሞኑን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የገለፁት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌድዮን ጢሞቲዎስ "በአግባቡ የተከለለ፣ የተሰመረ ወይም የተለየው ግን ከግማሽ በታች የሚሆነው ነው" ብለዋል።
አሰተያየታቸውን ለዶቼ ቬለ የሰጡ አንድ የቀጣናዊ ጉዳይ ተንታኝ፣ የሀገራቱ ድንበር በአግባቡ አለመካለል በቀጣናው "ቋሚ የሆነ የግጭት መነሻ እየሆነ ቆይቷል" ብለዋል። ይህም "አንዱ መንግሥት በጎረቤት ሀገር ላይ ያለውን መንግሥት ለመጣል አንድ መንገድ ሆኖም ቆይቷል" ሲሉ ጠቅሰዋል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ውስጥ ካሉ ሁሉም ሀገራት ጋር የምትዋሰን "ብቸኛ ሀገር" መሆኗን በሳምንቱ መጨረሻ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የገለፁት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌድዮን ጢሞቲዎስ፣ ይህ የድንበር እና የወሰን ጉዳይ "ትኩረት የሚፈልግ፣ ተጨማሪ ሰፊ" ያሉትንም ሥራ የሚጠይቅ ነዉ። አንዳንድ ሀገራት ይህንን የሚመለከት ኮሚሽን አቋቁመዉ ከየሀገራቱ ጋር "በዲፕሎማሲ ግንኙነት የተለየ፣ የታወቀ ድንበር እንዲኖር እንቅስቃሴ ያደርጋሉ" ያሉት ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ በዚህ ረገድ ብዙ ይቀራታል ብለዋል።
ሚኒስትሩ የማካለል ሥራዉን ለመሥራት መጀመርያ መለየት እና መጠናት ያለባቸው የዉስጥ ሥራዎች እንዳሉ ገልፀዉ በሂደት ከጎረቤት ሀገራት ጋር "ጉዳዩን አጀንዳ አድርገን መነጋገር፣ መግባባት ይጠይቃል" ሲሉም አስገንዝበዋል።አሰተያየታቸውን ለዶቼ ቬለ የሰጡት የቀጣናዊ ጉዳይ ተንታኝ ዶክተር አሰፋ ለዓከ የሀገራቱ ድንበር በአግባቡ አለመካለሉ በአካባቢው "ቋሚ የሆነ የግጭት መነሻ እየሆነ ቆይቷል" ብለዋል።ባለሙያው ይህ ሁኔታ የሚፈጥራቸው የግጭት እና ጦርነት ችግሮች በዚህ ቀጣና ይባሱ እንጂ የሁሉም የአህጉሩም ጭምር ነዉ።"ይህ በምስራቅ አፍሪካ የባሰ ሆነ እንጂ በመለ የአፍሪካ ሀገር ላይ የጦርነት አንዱ መነሻ እየሆነ ያለው እሱ ነው"
ጉዳዩን "በእቅድ ይዘን በቀጣይ ዓመታት መሥራት ያለብን ነዉ" ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚኑስትር ጌድዮን በመረጃ ላይ ተመስርቶ የሀገርን ጥቅም፣ ድንበር እና ሉዓላዊነት የሚያስከብር ሰፊ ሥራ" ከፊት ይጠብቃልም በሚል የመንግሥትን ዕቅድ ይፋ አድርገዋል።እንደ ዶክተር አሰፋ ለዓከ ግምገማ የአህጉራዊ ድርጅቱ ዉሳኔ ግን "መፍትሔ ሊሆን አልቻለም"የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የቀድሞ ቅኝ ገዢ ሀገራት በአህጉሩ ያሰመሩትን ድንበር ተቀብሎ የፀና አድርጎ የቀጠለ በመሆኑ የአብዛኞቹ ሀገራት ድንበር ነባር ሕዝቦችን ወዲህና ወዲያ የነጣጠለ፣ በተለያዩ ሀገራት ውስጥም ተለያይተው እንዲኖሩ ያደረገ ነው።
ሰለሞን ሙጬ
ነጋሽ መሐመድ
ኂሩት መለሰ