ከ 500 በላይ ሰዎች ምዕራብ ጉጂ ዞን በቁጥጥር ስር ዋሉ
ቅዳሜ፣ ሰኔ 15 2011የምዕራብ ጉጂ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አበራ ቡኖ ከዶቼ ቨለ ( DW ) ጋር ባደረጉት ቃል ምልልስ እንዳሉት ታጣቂዎቹና ተባባሪዎቻቸው ሰሞኑን በቁጥጥር ስር የዋሉት የኦሮሚያ ልዩ ሀይል ከአገር መከላከያ ሰራዊትና ከህብረተሰቡ ጋር በመቀናጀት ባደረጉት አሰሳ ነው።
ግለሰቦቹና ቡድኖቹ በህዝቡና በጸጥታ አባላቱ ትብብር የተያዙት በዞኑ የተለያዩ ወረዳዎችና ቀበሌያት ውስጥ በመዘዋወር በህብረተሰቡ ላይ የተለያዩ ጥቃቶችን በማድረሳቸው መሆኑን ዋና አስተዳዳሪው ተናግረዋል።
በቁጥጥር ስር ከዋሉት መካከል አንድ መቶ አስሩ በኦሮሞ ነፃነት ግንባር ስም ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ታጣቂዎች ሲሆኑ ቀሪዎቹ ደግሞ ታጣቂ ቡድኑን በተለያዩ መንገዶች ሲደግፉ የተደረሰባቸው መሆናቸውን ነው ዋና አስተዳዳሪ አቶ አበራ ቡኖ የጠቀሱት ።
ታጣቂዎቹ በምዕራብ ጉጂ ዞን ነዋሪዎችንና በአጎራብች ድንበሮች ላይ በሚገኙ የአማሮና የቡርጂ ማህበረሰብ አባላት ላይ የግድያ ፣ የዘርፋ እና የአስገድዶ መድፈር ድርጊቶችን ሲፈድሙ መቆየታቸውን ዋና አስተዳዳሪው አስታውሰዋል ።
ከተያዙት መካከል የወንጀል ድርጊቶችን የፈጸሙት ለህግ የሚቀርቡ ሲሆን ሌሎች ዝቅተኛ ተሳትፎ ያላቸው ግን የታድህሶ ስልጠና ወስደው ወደ ህብረተሰቡ የሚቀላቀሉ ይሆናል ብለዋል።
በአሁኑ ወቅትም ታጣቂዎቹን ከአካባቢው ጠራርጎ ለማስወጣትና የዞኑን ሰላም ለማረጋገጥ ሁጡራ የሚል ዘመቻ ተከፍቶ ተግባራዊ እየተደረገ እንደሚገኝም አቶ አበራ ቡኖ አመልክተዋል።
የምዕራብ ጉጂ ዞን መስተዳድር ያዝኳቸው ባላቸው ታጣቂዎች ዙሪያ አስከአሁን በኦሮሞ ነፃነት ግንባር በኩል የተሰጠ መግለጫም ሆነ ማስተባበያ የለም ። ዶይቸ ቬለ ( DW ) በጉዳዩ ላይ ያነጋገራቸው የኦሮሞ ነፃነት ግንባር ቃል አቀባይ አቶ ቶሌራ ዳባ ኦነግ በአሁኑ ወቅት ታጥቆ የሚንቀሳቀስ ሰራዊት የለውም ብለዋል።
የምዕራብ ጉጂ ዞንና በአጎራባች የአማሮና የቡርጂ አካባቢዎች ታጣቂዎች በተደጋጋሚ በሚፈፅሟቸው የደፈጣ ጥቃቶች በርካቶች ለሞት ፣ ለአካል ጉዳትና ለመፈናቀል መዳረጋቸው ይታወቃል ። በዚህም ምክንያት የኦሮሚያ ክልልና የፌደራሉ መንግስት ሰላማዊ ዜጎችን ከታጣቂዎች ጥቃት ለመጠበቅ ዳተኝነት አሳይተዋል የሚሉ ተደጋጋሚ ትችቶች እየቀረበባቸው ይገኛል።
ሸዋንግዛው ወጋየሁ
ልደት አበበ