ኮሮና፦ ዳግም የእንቅስቃሴ ገደብ በጀርመን
ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 27 2013ጀርመን ውስጥ ቊጥሩ እየጨመረ የመጣውን የኮሮና ተሐዋሲ ወረርሺኝ ለመቆጣጠር ይቻል ዘንድ፦ ቀደም ሲል የተጣለው የእንቅስቃሴ ገደብ ለተጨማሪ ሦስት ሳምንታት እንዲራዘም ተጠየቀ። የፊታችን እሁድ የሚያበቃው የእንቅስቃሴ ገደብ እስከ ጥር 23 ቀን፣ 2013 ዓ.ም ድረስ ነው እንዲራዘም የተወሰነው። በተለይ የኮሮና ተሐዋሲ በቀን ከአንድ ሺህ በላይ ሰዎችን ሕይወት ጀርመን ውስጥ መቅጠፍ መጀመሩ 16ቱ ክፍለ ሃገራት መሪዎች ላይ ጫናው እንዲበረታ አደርጓል። መሪዎቹ ከመራኂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ጋር ዛሬ በቪዲዮ ኮንፈረንስ መክረዋል። ጀርመን ውስጥ እስካሁን ድረስ በኮሮና ተሐዋሲ ምክንያት ከ34,000በላይ ሰዎች ጀርመን ውስጥ ሕይወታቸውን አጥተዋል። በተራዘመው ጊዜ ውስጥ ነዋሪዎች ከቤተሰብ ውጪ እንዳይገናኙ ተወስኗል። የዛሬው ውሳኔ በዋናነት ያተኮረው ምን ላይ ነው? የእንቅስቃሴ ገደቡ የተጣለው በእነማን ላይ ነው? ትምህርት ቤቶች እና አገልግሎት መስጫ ተቋማት እንቅስቃሴያቸው እንዴት ይሆናል?
ከአውሮጳ ኅብረት የወጣችው ብሪታንያም ጥብቅ የእንቅስቃሴ ገደብ ጥላለች። በአዲሱ አገደም መሠረት ማንኛውም ሰው እጅግ አስፈላጊ ለሆነ ጉዳይ ብቻ ነው ወደ ውጪ መውጣት የሚፈቀድለት። ብሪታንያ ውስጥ ነዋሪው፦ ወደ ሥራ አለያም ሐኪም ቤት ለመኼድ፣ ወይንም የምግብ ሸቀጦችን ለመግዛት ብቻ ነው መውጣት የሚፈቀድለት።
የአውሮጳ ግዛት ለአባል ሃገራቱ ነዋሪዎች ክፍት ከመሆኑ አንጻር ጀርመን ብቻዋን ጥብቅ የእንቅስቃሴ ገደብ ማድረጓ ውጤቱ ላይ ተጽእኖ አይኖረውም? ለአብት ያህል የከባድ ጭነት አሽከርካሪዎች በብዛት ወደ ጀርመን ይገባሉ ከጀርመንም ወደ ሌሎች የአውሮጳ ሃገራት ያቀናሉ። የዚህ ተጽእኖስ ውሳኔው ላይ ታሳቢ ተደርጓል?
ይልማ ኃይለሚካኤል
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ነጋሽ መሐመድ